Go to full page →

የአምልኮ ሰዓት MYPAmh 220

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትን ፍቅር ለማነሳሳትና ለማጠንከር በአብዘኛው የሚያስፈልገው የአምልኮ ሰዓትን መጠቀም ነው፡፡ የጠዋትና የምሽት የአምልኮ ሰዓቶች ከቀኑ ውስጥ እጅግ ጣፋጭና ጠቃሚ መሆን አለባቸው፡፡ በእነዚህ ሰዓቶች ወላጆችና ልጆች ከኢየሱስ ጋር ለመገናኘትና በቤታቸው ውስጥ የቅዱሳን መላእክትን መገኘት የሚጋብዙበት ጊዜ ስለሆነ የተረበሹና ደግነት የጎደላቸው አስተሳሰቦች ጣልቃ እንዲገቡ መፈቀድ የለባቸውም፡፡ በእነዚህ ሰዓቶች የሚቀርቡ አገልግሎቶች አጭርና በሕይወት የተሞሉ፣ ከሁኔታው ጋር የተጣጣሙና ከጊዜ ወደ ጊዜ የተለያዩ ዓይነት መሆን አለባቸው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ሁሉም ይሳተፉ፣ የእግዚአብሔርን ሕግ ይማሩ፣ ሁል ጊዜም ይደጋግሙት፡፡ አንዳንድ ጊዜ የሚነበበውን ነገር እንዲመርጡ ቢፈቀድላቸው የልጆችን ፍላጎት ሊጨምር ይችላል፡፡ ከንባቡ በኋላ ጥያቄ ጠይቁአቸው፣ እነርሱም እንዲጠይቁ ፍቀዱላቸው፡፡ ትርጉሙን ሊያብራራ የሚችል ማንኛውንም ነገር ጥቀሱላቸው፡፡ አገልግሎቱ በጣም ባልረዘመ ጊዜ ሕፃናት በጸሎት ይሳተፉ፤ አንድ ቁጥርም ቢሆን በዝማሬ አብረው ይዘምሩ፡፡ MYPAmh 220.1

እንደዚህ ዓይነቱ አገልግሎት መሆን የሚገባውን ሆኖ እንዲገኝ ሐሳባችን እንዲዘጋጅ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ወላጆች በየቀኑ ከልጆቻቸው ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ጊዜ መውሰድ አለባቸው፡፡ ይህንን ማድረግ ደግሞ ጥረትን፣ ማቀድንና መስዋዕትነትን እንደሚጠይቅ ጥርጥር የለውም፡፡ ነገር ግን ለዚህ የሚደረግ ጥረት ታላቅ ዋጋ አለው፡፡ Education, P. 186. MYPAmh 220.2