Go to full page →

የነፍስን መንገዶች በደንብ ጠብቁ MYPAmh 185

“ልብህን አጥብቀህ ጠብቅ የሕይወት ጉዳዮች መውጫ ከእርሱ ነውና።” የሚለው የጠቢቡ ሰው ምክር ነው። ሰው “በልቡ እንደሚያስበው እንደዚያው ነው።” ልብ በመለኮታዊ ፀጋ ከልታደሰ በስተቀር የህይወት ንፅህናን መሻት ከንቱ ነው። ከክርስቶስ ፀጋ ውጭ የከበረና መልካም ባህርይ ለመገንባት የሚጥር ሰው ቤቱን በተንሸራታች አሸዋ ላይ እየገነባ ነው። የፈተና ኃይለኛ ማዕበል ሲያገኘው በርግጠኝነት ይፈርሳል። “ጌታ ሆይ ንፁህ ልብ ፍጠርልኝ፣ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስ” የሚለው የዳዊት ጸሎት የእያንዳንዱ ነፍስ ልመና መሆን አለበት። የሰማያዊ ሥጦታ ተካፋዮች በመሆናችን “በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል በመጠበቅ” ወደ ፍጽምና መሄድ አለብን። MYPAmh 185.1

ሆኖም ፈተናን ለመቋቋም የምንሰራው ሥራ አለ። ለሰይጣን ወጥመዶች ግዳይ ከመሆን ማምለጥ የሚፈልጉ ሰዎች የነፍስን መንገዶች መጠበቅ አለባቸው። ንፁህ ያልሆኑ አስተሳሰቦችን ወደ አእምሮ የሚያመጡ ነገሮችን ከማንበብ፣ ከማየትና ከመስማት መቆጠብ አለባቸው። አእምሮ የነፍሳት ጠላት የሆነው በሚያመጣቸው እያንዳንዱ ጉዳዮች እንዲዛባ መተዉ የለበትም:: ሐዋሪያው ጴጥሮስ “ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁ በመጠን ኑሩ።….እንደሚታዘዙ ልጆች ባለማወቃችሁ አስቀድሞ የኖራችሁበትን ምኞት አትከተሉ! የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ::“ይለናል። ጳውሎስ ደግሞ “ንፁህ የሆነውን ነገር ሁሉ፣ ታማኝነት ያለበትን ነገር ሁሉ፣ እውነት የሆነውን ነገር ሁሉ፣ ተወዳጅ የሆነውን ነገር ሁሉ፣ ጽድቅ የሆነውን ነገር ሁሉ፣ መልካም ዜና ያለበትን ነገር ሁሉ፣ መልካም ሥራም ቢሆን እነዚህን ነገሮች አስቡ።” ይለናል:: ይህ ደግሞ ልባዊ ጸሎትንና ሁልጊዜ ነቅቶ መጠበቅን ይጠይቃል። አእምሮን ወደ ላይ በሚስብና ንጹህና ቅዱስ በሆኑ ነገሮች ላይ እንዲያድር በሚያደርግ የመንፈስ ቅዱስ ኃይል መመራት አለብን። የእግዚአብሔርን ቃል ተግተን ማጥናት አለብን። “ጎልማሳ መንገዱን በምን ያነፃል፣ እንደ ቃልህ በመኖር ነው።” ባለ መዝሙሩ ዳዊት “አንተን እንዳልበድል ቃልህን በልቤ ውስጥ ደበቅሁ” ይላል። Patriarchs and prophets, P.460. MYPAmh 185.2