Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

ሥነ - ትምህርት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ 23—የመዝናኛ ጉዞ

    «ለሁሉም ጊዜ አለው»EDA 230.1

    በመዝናናትና በሳቅ ጨዋታ መካከል ልዩነት አለ፡፡ ስሙ እንደሚያመለከተው የጉብኝት ጉዞ ወደ ሽርሽር በሚካሄድበት ጊዜ ጥቅሙ ብርታት ወደ መስጠትና ወደ ግንባታ ያዘነብላል፡፡ ከዘወትር የዕለት ሥራና ተግባራችን ላይ አስነስቶ ለአእምሮና ለአካል ተሃድሶ የሚሰጥ ሲሆን በዚህም የወደፊቱን የሕይወት ተግባራችንንም ከልብ እንድንሠራ በአዲስና ኃይለኛ መንፈስ እንድንመለስ ያደርገናል፡፡ በሌላ በኩል ግን ሳቅና ጨዋታ ለደስታ ሲባል ብቻ የሚደረግና ብዙ ጊዜም ከመጠን የሚያልፍ በመሆኑ ለጠቃሚ ተግባር የሚያስፈልገንን ኃይል ይወስደውና በሕይወት ውስጥ በትክክል ሊሳካልን ለሚገባው ነገር እንቅፋት ሲሆን ይታያል፡፡EDA 230.2

    ጠቅላላ ሰውነታችን ለሥራ የተፈጠረ ነው፡፡ የአካላዊ ኃይሎቻችን በነቃ እንቅስቃሴ ጤንነት ካልተጠበቀ የአእምሮ ችሎታዎች በሙሉ ኃይላቸው ጥቅም ላይ ሊውሉ አይችሉም፡፡ በትምህርት ክፍል ውስጥ ዘወትር የሚታየው የአካል ድክመት ከሌሎች ጤናማ ካልሆኑ ሁኔታዎች ጋር ተዳምሮ በተለይ ተክለአሟቸው ደካማ በሆኑ ሕፃናት ላይ እንደሙከራ ጣቢያ ዓይነት ነው የሚሆነው፡፡ በቂ አየር የለም ያልተስተካከሉ መቀመጫዎች ተፈጥሮአዊ ያልሆኑ መወለጋገድን ያስከትላሉ፡፡ በመሆኑም የሳምባዎችንና የልብን የሥራ እንቅስቃሴም ያውካሉ፡፡ ያስተጓጉላሉ፡፡ እዚህ ላይ እንግዲህ ትንንሽ ልጆች የቆሸሸ ምናልባትም በበሽታ ጀርሞች የተበከለ አየር እየሳቡ በየቀኑ ከሦስት እስከ አምስት ሰዓት ለሚሆን ጊዜ ይቆያሉ ማለት ነው፡፡ ት/ቤቱ የዕድሜ ልክ በሽታ መሠረት መጣያ ሆኗል ቢባል አያስደንቅም፡፡ ከአካል ብልቶች ሁሉ እጅግ ልስልስ በጣም ትንሽ በሆነ ነገር በቀላሉ ሊጐዳ የሚችል ስስ የሆነው አእምሮአችን፤ የአጠቃላይ ሥርዓቱና የነርቮች ኃይል ምንጭ የሆነው ይህ ብልት ከሁሉም የበለጠው ጉዳት ይደርስበታል፡፡ ባልደረሰ አቅማቸው ከመጠን በላይ የሆነ ተግባር እንዲያከናውኑ፤ ለዚያውም ጤናማ ባልሆነ ሁኔታዎች ውስጥ እንዲሠሩ ሲገደዱ አእምሮአቸው ይዝላል፡፡ ብዙ ጊዜም ዘላቂ ጉዳት ይከተላል፡፡EDA 230.3

    ልጆች በቤት ውስጥ ተዘግቶባቸው ብዙ መቆየት የለባቸውም፡፡ ወይም ጥሩ የአካል እድገት መሠረት እስከሚጣልላቸው ድረስ ጠበቅ ያለ ጥናት በራሳቸው ጥረት ብቻ እንዲያጠኑ መለቀቅ አይኖርባቸውም፡፡ ከልጁ ሕይወት ውስጥ ለመጀመሪያዎቹ ስምንትና አሥር ዓመታት የተሻለ ትምህርት ቤት የሚሆነው መቧረቂያ ሜዳና የጓሮ አትክልት ቦታ ነው፡፡ በዚያም እጅግ ምርጥ መምህር የምትሆነው እናት ስትሆን እጅግ ድንቅ የትምህርት መጽሐፍ የሚሆነው ደግሞ ተፈጥሮ ይሆናል፡፡ ልጁ ትምህርት መከታተልን በሚገባ ከቻለ በኋላ እንኳ በመጽሐፍ ላይ ለሚገኝ እውቀት ከሚደረገው ጥንቃቄ የበለጠ ለጤናው እንክብካቤ ሊደረግ ይገባዋል፡፡ ለአካልና ለአዕምሮ እድገት በሚበጅ ተስማሚ የአካባቢ ሁኔታዎች ውስጥ መኖር አለበት፡፡EDA 231.1

    የአካል እንቅስቃሴ ለማድረግ በሚፈልግበት ጊዜ በሚያጋጥም የንፁህ አየር እጥረት የሚቸገሩት ልጆች ብቻ አይደሉም፡፡ በከፍተኛ ደረጃም ሆነ በዝቅተኛ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ እነዚህ አስፈላጊ ነገሮች ዘወትር ችላ ይባላሉ፡፡ አንዳንድ ተማሪ በአንድ ጠባብ ክፍል ውስጥ ከቀን ወደ ቀን መጽሐፎች ላይ አጐንብሶ ወይም ተኝቶ ሙሉ ትንፋሽ በጥልቀት ንፁህ አየር እየወሰደ ለመተንፈስ እንደማይችል ደረቱ ተጣብቆ የደም ዝውውሩም እየተጓተተና እግሮቹ ቀዝቅዘው ጭንቅላቱ በትኩሳት ግሎ ይመጣል፡፡ የተመጣጠነ ምግብ ያልተመገበ ልጅ ጡንቻዎቹ ይዳከማሉ፡፡ አጠቃላይ ሥርዓቱም መንፈሱም ይዳከማል በሽተኛም ይሆናል፡፡ እንዲህ ዓይነት ተማሪዎች እድሜ ልካቸውን ዋጋ ቢስ ይሆናሉ በተሻለና ተገቢ በሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ ዘወትር ፀሐይና በቂ አየር ባለበት ቦታ እንቅስቃሴ እያደረጉ ጥናታቸውን ቢከታተሉ ከፍተኛ የአካልና የሕሊና ብርታት በሚጠይቅ ትምህርት ቤት ሊገቡ ይችላሉ፡፡EDA 231.2

    ባለችው የተወሰነች ጊዜና እንዳቅሙ ባገኘው መሣሪያ አማካይነት ትምህርት ለማግኘት የሚታገል ተማሪ ለአካላዊ እንቅስቃሴ የሚያጠፋው ጊዜ ከብክነት እንደማይቆጠር ሊገነዘብ ይገባዋል፡፡ ያለ ማቋረጥ በመጽሐፎች ላይ ብቻ የሚያተኩር ሰው ከጊዜ በኋላ አእምሮው እረፍትና መታደስ ስለሚጐድለው አዲስ ኃይል ያጣል፡፡ ለአካል መዳበር ተገቢውን ትኩረት የሚሰጡ ጊዜአቸውን ሁሉ ለጥናት ብቻ ከሚያውሉት በበለጠ በትምህርት መስክ ከፍተኛ ብልጫ ያሳያሉ፡፡EDA 232.1

    አዕምሮ አንድ የሐሳብ መስመርን ብቻ ሲከታተል ሚዛኑ ያጋድጋል፡፡ እያንዳንዱ የአእምሮና የአካል ኃይሎች በደህና ሁኔታ እኩል፤ ሊንቀሳቀሱ የሚችሉት ሐሳብም በተለያዩ ትምህርተ ጉዳዮች ላይ ሲያርፍ ነው፡፡EDA 232.2

    አካላዊ ድክመት የአእምሮ ደካማነትን ብቻ ሳይሆን ወኔ ቢስም ያደርጋል፡፡ አእምሮን ከአጠቃላይ የሰውነት ሥርዓት ጋር የሚያገናኙ ነርቮች ሰማይን ከሰው ጋር የሚያገናኙና ውስጣዊ ሕይወቱን የሚነኩ አስተላላፊ መሣሪያዎች ናቸው፡፡ በነርቭ ሥርዓት ውስጥ ያለውን የኤሌክትሪክ ዝውውር አንድ ነገር ቢያሰናክለው ፤ በዚህም ዋናዎቹን የአእምሮ ኃይሎች ቢያዳክሙና የሕሊናን ንቃት ቢቀንስ የሞራልን (ወኔን) ባሕሪይ ለማነሳሳት የበለጠ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡EDA 232.3

    እንደገናም ከልክ ያለፈ ጥናትም ብዙ ደም ወደ አእምሮ እንዲፈሰስና የመቆጣጠር ችሎታን ቀንሶ በሽተኛ ወፈፌ ወደ መሆን፣ ንግግሩና ሐሳቡ የሚለወጥ፤ የሚዘበራረቅ በሽተኛ በደመ ግፊትም የሚጠቃ ይሆናል፡፡ ስለዚህም በኃጢአት በሩ ክፍት ይሆናል፡፡ ዛሬ በዓለም ላይ ለተስፋፋው የቅሌት ማዕበል እና መማለጃ ዋናው ምክንያት የአካልን ኃይሎች በትክክል ጥቅም ላይ ካለማዋል ወይም ፈጽሞ በሥራ ላይ ካለማዋልም ነው፡፡ «ኩራት እጅግ በብዙ ምግብ ሆድን መሙላትና እጅግም አለሥራ ቦዝኖ መቀመጥ፡፡» ለሶዶም ጥፋት ዋነኛ ምክንያቶች እንደበሩ ሁሉ በዚህ ትውልድ ውስጥ ላለው የሰው ልጅ እድገትም ዋነኛ ጠላት ናቸው፡፡EDA 232.4

    መምህራን እነዚያን ነገሮች አስተውለው ተማሪዎቻቸውን በነዚህ መስመሮች ሊመሯቸው ይገባል፡፡ ተማሪዎችህን ትክክለኛ ኑሮ በትክክለኛ አስተሳሰብ ላይ እንደሚመሠረትና ለሐሳብ ንጽህና ደግሞ አካላዊ እንቅስቃሴ ዋና መሠረት መሆኑን አስተምራቸው፡፡EDA 233.1

    ለተማሪዎቻቸው ተስማሚ የሚሆን የሽርሽር ቦታ የማግኘቱ ጉዳይ ለመምህራን ዘወትር አስቸጋሪ ጥያቄ ነው፡፡ ጠቃሚ ቦታ ይይዛል፡፡ ነገር ግን በጥንቃቄ ቁጥጥር ካልተደረገበት ብዙ ጊዜ መጠኑን ያልፋል፡፡ ብዙ ወጣቶች በአካል ማጠንከሪያ (ጅምናስቲክ) ቦታ በራሳቸው የመሰላቸውን ያለአቅማቸው እየሠሩ የእድሜ ልክ ጉዳት የደረሰባቸው አሉ፡፡EDA 233.2

    በአካል ማሰለጠኛ ቦታ ውስጥ የስፖርት እንቅስቃሴ ማድረግ፣ ምንም ያክል በጥሩ ሁኔታ ቢመራ እንኳ ንፁህ አየር እንደልብ የሚገኝበት የሽርሽር መዝናኛ ቦታ የሚሰጠውን ደስታ ሊያበረክትልን አይችልም፡፡ እናም ለዚህ ትምህርት ቤቶቻችን የተሻለ አማራጭ አዘጋጅተው ማቅረብ አለባቸው፡፡ ተማሪዎቹ አዲስ ኃይልና ብርታት የሚሰጣቸው ልምምድ ማድረግ አለባቸው፡፡ ከመቦዘንና ዓላማ የለሽ ከመሆን ይልቅ በመዝናኛ ቦታዎች የሚፈፀሙ ጥቃቅን ጥፋቶች ይሻላሉ፡፡ ይሁንና አብዛኛዎቹ ሩጫና ዝላይን የመሳሰሉት የስፖርት ዓይነቶች አዝማሚያ ለወጣቶች ደህንነት ከልባቸው ለሚያስቡ ሁሉ የጭንቀት ትምህርት ነው፡፡ መምህራን የእነዚህን የስፖርት ዓይነቶች ማራኪነት ሲያስቡ ተማሪው በክፍል ውስጥ በትምህርቱ የሚኖረውን እድገትና ለወደፊቱ ሕይወቱ መሳካትም በጣም ይጨነቃሉ፡፡ አብዛኛው ጊዜውን የሚወስዱበት ግጥሚያዎች አእምሮው ወደጥናት እንዳያዘነብል ያደርጉታል፡፡ ወጣቱን ተግባራዊና ልባዊ ለሆነ ዘላቂ ሕይወቱ እንዲዘጋጅ የሚጠቅሙ አይደሉም፡፡ ማራኪነታቸው ወደ ብልህነት ቀናትነና ለጋስነት ወይም ወደ ሰብዓዊነት የሚያዘነብል አይደለም፡፡EDA 233.3

    በሕዝብ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆኑ እንደ እግር ኳስ እና ቦክስ የመሳሰሉ ጨዋታዎች የጭካኔ ት/ቤቶች እየሆኑ መጥተዋል፡፡ በጥንታዊት ሮም ይታዩ የነበሩትን ባህሪያት መልሰው እያዳበሩ መጥተዋል፡፡ በአሸናፊነት የበላይ የመሆን ፍቅር፤ ጨካኝና ኃይለኛ በመሆናቸው ብቻ መኩራት ለሕይወት ፍፁም ሳያስቡ መቻኮል በወጣቱ ላይ ሞራል የሚነካ አስደንጋጭ ተጽዕኖ እያደረጉበት ነው፡፡EDA 234.1

    ሌሎች ጨዋታዎች ምንም እንኳን ጭካኔ የተሞላባቸው ባይሆኑም የሚሰነዘርባቸው ተቃውሞ መለስተኛ ነው፡፡ ምክንያቱም ከሚወስዱት ረዥም ጊዜ አንፃር ብቻ ነው፡፡ የደስታና ፈንጠዝያ ስሜትን ይቀሰቅሳሉ፡፡ በመሆኑም ጠቃሚ ሥራ ወይም ቁምነገርን ማጥላትና ተግባራዊ እንቅስቃሴና ኃላፊነትን መሸሽን ያመጣሉ፡፡ በሕይወት ውስጥ ለቁመ ነገር ሥራና ለጨዋታ የሚሆነውን ጊዜ ልክ ማጣትን በመጠኑ የመደሰትን ሐሳብ ወደ ማጥፋት ያዘነብላሉ፡፡ በመሆኑም ከመጥፎ ውጤታቸው ጋር ለማታለልና ለሕገወጥነት በሩ ይከፈታል፡፡EDA 234.2

    በተለምዶ እንደሚደረገው የጭፈራ የጨዋታ ድግሶች ለትክክለኛ የአእምሮ ወይም የባህሪ እድገት እንቅፋት ነው፡፡ የዘፈቀደ ነፃ ጓደኝነት፣ የብኩንነት ልማዶች፣ ደስታ ለማግኘት ሲባል የሚደረጉ ጨዋታዎች አብዛኛውን ጊዜ ጠቅላላ ሕይወትን ለጥፋት የሚያዘጋጅ፣ የማታለያ ማኅበራት ናቸው፡፡ በእንዲህ ዓይነት የጨዋታ ቦታዎች ወላጆችና መምህራን መልካምና ሕይወት ሰጪ ወደሆነ መንገድ መመለስ ይችላሉ፡፡EDA 234.3

    በዚህና በሌሎች ደህንነታችን በሚመለከቱ ነገሮች ሁሉ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡ በጥንት ዘመናት በእግዚአብሔር አመራር ሥር በነበሩ ሰዎች ዘንድ ኑሮ ቀላል ነበር፡፡ ወደተፈጥሮ በጣም ከልባቸው ተጠግተው ይኖሩ ነበር፡፡ ልጆቻቸውም በወላጆቻቸው ሥራ ውስጥ አብረው እየተካፈሉ የተፈጥሮን መዝገብ ቤት ውበትና ምስጢሮች ያጠኑ ነበር፡፡ ፀጥ ባለ ሜዳና ጫካ ውስጥም በእነኛ ግዙፍ እውነቶች ላይ ልቦናቸውን አሰባስበው ያተኮሩ እንደቅዱስ እምነት ከትውልድ ወደ ትውልድም እየተሸጋገሩ ሊወርዱላቸው ችለዋል፡፡EDA 235.1

    ባሁኑ ዘመን፣ ሕይወት ወይም ኑሮ ሰው ሰራሽ እየሆነ መጥቷል፡፡ የሰው ልጅም ተዋርዷል፡፡ ወደ እነኛ ጥንታዊ ቀላል ልማዶች ሙሉ ለሙሉ ብንመለስ ኖሮ ስማቸው እንደሚያመለክተው የመዝናኛ የሽርሽር ጉዞ ጊኔአችንን ትምህርት የምናገኝበት ባደረጉልን ነበር፡፡ እውነተኛ የአካል የአእምሮና የነፍስ ግንባታ ወቅቶች በሆኑልን ነበር፡፡EDA 235.2

    ከመዝናኛ የጉብኝት ሰዓት ጥያቄ ጋር የቤታችንና የትምህርት ቤታችን አካባቢዎች ብዙ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ ቤት ወይም ትምህርት ቤት ለመሥራት በሚደረግ የቦታ ምርጫ እነዚህ ነገሮች መታሰብ አለባቸው፡፡ የአእምሮና የአካልን ደህንነትን ከገንዘብ ወይም ከኅብረተሰብ ልማዶችና አስተሳሰቦች አስበልጠው ለሚመለከቱ የተፈጥሮን ትምሀርት ሰጪነት ጠቀሜታ መሻት፤ ተፈጥሮንም በዙሪያቸው አድርገው እመሃሏ ውስጥ መዝናናት አለባቸው፡፡ እያንዳንዱ ትምህርት ቤት ለተማሪዎቹ ያትክልት ቦታ እና ጫካ ኖሮት ለመስክ ሥራና ለእንጨት ሥራዎች የሚወጡበት ምቹ ሁኔታ ቢኖር ለትምህርቱ ሥራ በእጅጉ ይረዳል፡፡EDA 235.3

    የሽርሽር መዝናኛን በተመለከተ ተማሪው ጥሩ ትምህርት ወይም ጠቃሚ ውጤቶችን ሊያገኝበት የሚችለው የመምህሩ የግል ትብብር ነው፡፡ እውነተኛ መምህር ለአንድ የግል ጓደኛው እንደሚያበረክተው ዓይነት ስጦታ ለተማሪዎቹም ጥቂት ስጦታዎ ማካፈል ይችላል፡፡ በአዋቂ ሰዎች ላይ እንደምናየው ሁሉ በወጣቶችና በልጆች ላይ ደግሞ በርህራሄ ስንቀርባቸው ምን ያክል ይበልጥ ልንረዳላቸው እንችላለን፡፡ የበለጠ እንጠቀመ ዘንድ ደግሞ በቅርብና በትክክል ልናስተውላቸው ይገባናል፡፡ በመምህሩና በተማሪው መካከል የሚኖረውን የርህራሄ ትስስር ለማጠንከር ከትምህርት ክፍል ውጪ የሚደረጉ አስደሳች ማኅበራዊ ግንኙነቶች ጥቂቶቹ መንገዶች ናቸው፡፡ በአንዳንድ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በተማሪዎች የመዝናኛ የሽርሽር ሰዓት መምህሩ ሁልጊዜም ከጐናቸው አይጠፋም፡፡ በእቅዶቻቸው ላይ አብሮ አንድ ላይ ነው፡፡ በሽርሽር አብሯቸው ይወጣል፡፡ በማንኛውም እንቅስቃሴአቸው ሁሉ ከእነርሱ ጋር አብሮ እንደ አንድ ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት አሠራሮችና አጠቃላይ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ቢለመዱ ለትምህርት ቤቶቻችን ሁሉ መልካም በሆነ ነበር፡፡ ከመምህሩ የሚፈለገው መስዋዕትነት እጅግ ብዙ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በኋላ የድካሙን ዋጋ እጅግ ብዙ ያተርፍበታል፡፡EDA 236.1

    ለሌሎች ጠቃሚ ረዳት ለመሆን እንደሚያስችላቸው ዓይነት የመዝናኛ ጉዞ ለወጣቶችና ለልጆች ታላቅ በረከት የሚሆን ሌላ ለራሳቸው ብቻ የሚሆን ጉዞ የለም፡፡ ወጣቶች ንቁና በተፈጥሮም የሚገባቸው ስለሆኑ ለሚቀርብላቸው አስተያየት ቀና የሆነ ዕቅድ በሚዘጋጅበት ጊዜ መምህሩ የትምሀርት ቤቱን ቅጥር ግቢና ክፍሎቹን ሁሉ የማስዋብ ፍላጐት እንዲነቃቃ ያድርግ፡፡ ውጤቱ እጥፍ ጠቀሜታ ይኖረዋል ተማሪዎች ራሳቸው ያስጌጡትን ለማበላሸት ወይም ለማጥፋት አይፈልጉም፡፡ ንፁህ ስሜት፣ ሥርዓትን ማፍቀር እና ለሁሉ ነገር ጥንቃቄ ወስዶ የመንከባከብ ልምድ ይዳብራል፡፡ የጓደኝነትና የትብብር መንፈስ ስለሚያድግባቸው ተማሪዎቹ የእድሜ ልክ በረከት ያገኛሉ፡፡EDA 236.2

    እንዲሁም ደግሞ መሸከም ሆነ በጫካ ውስጥ ለሚሰጥ የአትክልት ሥራ ወይም የጉብኝት ትምህርት አዲስ ፍላጐት እንዲያድርባቸው መደረግ አለበት፡፡ ይህም ተማሪዎቹ ከእነዚህ አስደሳች ስፍራዎች ተገልለው ያሉትን እንዲያስታውሱና ለማበረታታትና ከእነርሱም ጋር በተፈጥሮ ውስጥ የሚገኙትን ውብ ነገሮች ለመጋራት እንዲችሉ ነው፡፡EDA 237.1

    ድንቅ መምህር ተማሪዎቹ የጥሩ ረዳትነት ተግባር እንዲያከናውኑ ለማድረግ ብዙ አጋጣሚዎችን ያገኛል፡፡ በተለይም መምህሩ በትንንሽ ልጆች ዘንድ ሙሉ እምነታቸውን ሊጥሉበት የሚችሉና የሚያከብሩትም ይሆናል፡፡ በቤት ውስጥ ስለሚያደርጉት እርዳታ፣ በየቀኑ በሚኖርባቸው ግዳጅ ላይ ስለሚጠበቅባቸው ታማኝነት፣ ለታመሙ ሰዎች ወይም ለድሆች ስለሚሰጡት ግልጋሎት፤ መምህሩ ከሚሰጣቸው ማንኛውም ዓይነት አስተያየት አንዷ እንኳ ያለፍሬ መሬት ጠብ አትልም፡፡ እናም በዚህ ምክንያት እጥፍ ፍሬ ይገኛል፡፡ መልካሙ አስተያየት መልሶ በደራሲው ላይ ይሠራል፡፡ በወላጆች በኩል ምስጋናና ትብብር በአፀፋው ሲመጣለት የመምህሩን ሸክም ያቀልለታል መንገዱንም ያበራለታል፡፡EDA 237.2

    ለሽርሽርና ለአካል ጥንካሬ ብቻ የሚሰጥ የትምህርት ትኩረት አንዳንድ ጊዜ ያለ ጥርጥር መደበኛውን የትምሀርት ሥራ እንደሚቋረጥ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ያ የተቋረጠ ጊዜ ይኸን ያክል መሰናክል የሚፈጥር አይደለም፡፡ አእምሮንና አካልን በአዲስ ኃይል በመሙላት በኩል ራስን ያለመውደድ መንፈስ እንዲያድርባቸው በሞግዚትነት መርዳት፤ መምህራንና ተማሪዎች በዘወትር የጋራ ፍላጐት ትስስርና የወዳጅነት ሕብረትን በመፍጠር የሚባክነው ጊዜና ጉልበት በፍጥነት በመቶ እጥፍ ይክሳል፡፡ ለወጣቶች ዘወትር የአደጋ ምንጭ የሚሆነው ረፍት የለሽ ኃይላቸው በዚህ ዓይነት ወጣ የሚልበት ሲያገኝ የተባረከ መተንፈሻ ይሆንለታል፡፡ ለክፉው እንደመከላከያ ሆኖ ያገለግል ዘንድ ቁጥር ስፍር ከሌላቸው ሕጐችና የሥርዓት ደንቦች ይልቅ አአምሮን አስቀድሞ በመልካም ነገር መሙላት የበለጠ ጠቀሜታ አለው፡፡ EDA 237.3

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents