Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

አእምሮ፣ባሕርይና ማንነት፣ክፍል 1

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ 31—የወጣቶች ችግሮች

    ወጣቶች ተቀባይና በተስፋ የተሞሉ ናቸው።--ወጣቶች ተቀባይ፣ ትኩስ፣ ታታሪና በተስፋ የተሞሉ ናቸው። ራስን መስዋዕት የማድረግን በረከት አንዴ ከቀመሱ ያለ ማቋረጥ ከታላቁ መምህር ካልተማሩ በቀር አይረኩም። ለጥሪው ምላሽ በሚሰጡ ሰዎች ፊት እግዚአብሔር መንገዶችን ይከፍታል። --6T 471 (1900). {1MCP 281.1}1MCPAmh 229.1

    ወጣቶች የህይወት መዳረሻቸውን መምረጥ አለባቸው።--እያንዳንዱ ወጣት በልጅነት ዕድሜው ዋጋ በሰጣቸው ሀሳቦችና ስሜቶች የራሱን የህይወት ታሪክ እየወሰነ ነው። በወጣትነት ጊዜ የተመሰረቱት ትክክለኛ፣ በጎ፣ የጀግንነት ልማዶች የባህርይ አካል ይሆኑና እንደተለመደው ግለሰቡ በሕይወት ዘመን የሚሄድበትን መንገድ ያመለክታሉ። ወጣቶች እንደ ምርጫቸው ጨካኝ ወይም በጎ አድራጊ ሊሆኑ ይችላሉ። በተመሳሳይ ሁኔታ እውነተኛና የከበረ ሥራ በመስራት ወይም ታላላቅ ወንጀሎችንና ክፋቶችን በመስራት ሊታወቁ ይችላሉ። --ST, Oct 11, 1910. (CG 196.) {1MCP 281.2}1MCPAmh 229.2

    የአእምሮና የግብረገብ ድክመትን የሚያስከትል ስልጠና።--ችሎታቸውና አስተሳሰባቸው በሚፈቅደው ልክ እንዲያስቡና እንዲሰሩ፣ በዚህም መንገድ በአስተሳሰብ፣ በስሜት፣ ራስን በማክበር እና ለመስራት ባላቸው ችሎታ በመታመን እንዲያድጉ በትክክል ሳይመሩአቸው የሚሰጥ ጥብቅ የወጣቶች ስልጠና በአእምሮና በግብረገብ ኃይል ደካማ የሆነ ክፍል ይፈጥራል። በዓለም ውስጥ የራሳቸውን ድርሻ ለመወጣት በሚቆሙበት ጊዜ እንደ እንስሶች የመሰልጠናቸውንና ያለመማራቸውን እውነታ ይገልጣሉ። ፈቃዶቻቸው ከመመራት ይልቅ ጭካኔ ላለበት ለወላጆችና ለመምህራን ቅጣት ለመገዛት ተገዶአል። --3T 133 (1872). {1MCP 281.3}1MCPAmh 229.3

    አእምሮ ሕይወትን ለመግዛት መማር አለበት።--ልጆች ኃይሎቻቸውን ሁሉ ወደ መቆጣጠር ሊመራ የሚችል ብልህ የሆነ ፈቃድ አላቸው። የማይናገሩ እንስሳት የማገናዘብና የአእምሮ እውቀት ስለሌላቸው መሰልጠን ያስፈልጋቸዋል። ነገር ግን ሰብአዊ አእምሮ ራስን መቆጣጠርን መማር አለበት። እንስሳት በጌታቸው ቁጥጥር ሥር ሆነው ለእርሱ ተገዥ እንዲሆኑ የሚሰለጥኑ ሲሆን አእምሮ ግን ሰብአዊ ፍጡርን ለመግዛት መማር አለበት። ጌታው ለእንስሳው እንደ አእምሮ፣ ውሳኔ ሰጭና የፈቃድ ኃይል ነው። ልጅም ልክ እንደ እንስሳ የራሱ ፈቃድ የሌለው እንዲሆን ተደርጎ ሊሰለጥን ይችላል። ግለሰብነቱ እንኳን ሳይቀር ሥልጠናውን በበላይነት በሚቆጣጠር ግለሰብ ውስጥ ሊጨፈለቅ ይችላል፤ ፈቃዱ፣ በሁሉም ግቦችና ዓላማዎች፣ ለመምህር ፈቃድ ተገዥ ነው። {1MCP 282.1}1MCPAmh 229.4

    በዚህ መልክ የተማሩ ልጆች ሁል ጊዜ በሞራል ጉልበትና በግል ኃላፊነት ጉድለት ያለባቸው ይሆናሉ። በምክንያት ወደ መርህ እንዲንቀሳቀሱ ትምህርት አልተሰጣቸውም፤ ሌላ ሰው ሲቆጣጠራቸው ስለነበር አእምሮአቸው በመስራት እንዲሰፋና እንዲጠነክር ዕድል አልተሰጠውም። አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ እጅግ ጠንካራ የሆኑ ኃይሎቻቸውን ሥራ ላይ ለማዋል ልዩ የሆኑ የሰውነት አቋሞቻቸውንና የአእምሮ ችሎታዎቻቸውን ባገናዘበ ሁኔታ አልተመሩም፣ ስነ-ሥርዓትንም አልተማሩም። አእምሮ ማደግ እስከሚችልበት መጠን እንዲደርስ ሁሉም ኃይሎች ሥራ ላይ መሆን እንዲችሉና ከአንዱ የጥንካሬ ደረጃ ወደ ሌላኛው መሻገር እንዲችሉ መምህራን በዚህ ቦታ ሳይቆሙ ደካማ የሆኑ ኃይሎችን ለማሳደግ የተለየ ትኩረት መስጠት አለባቸው።--3T 132 (1872). {1MCP 282.2}1MCPAmh 230.1

    ብዙዎች ለራሳቸው ማሰብ የማይችሉ ናቸው።--ልጆችን ሥነ- ሥርዓት እንዲጠብቁ ሲያሰለጥኑ በደንብ የሰለጠኑ የሚመስሉ ብዙ የልጆች ቤተሰቦች አሉ፤ ነገር ግን ሕጎችን እንዲያወጡ አድርጎአቸው የነበረው ሥርዓት ሲጣስ ለራሳቸው ማሰብ፣ መስራት ወይም መወሰን የማይችሉ ይመስላሉ። እነዚህ ልጆች ለራሳቸው በከፍተኛ ደረጃ ማሰብና መተግበር በሚገባቸው ነገሮች ላይ እንዳያስቡና እንዳይተገብሩ ተከልክለው ለረዥም ጊዜ በብረት በትር ሥር ስለነበሩ የራሳቸውን አመለካከት ለመያዝና በራሳቸው ውሳኔ ለመንቀሳቀስ በራሳቸው ላይ እምነት የላቸውም። {1MCP 282.3}1MCPAmh 230.2

    የራሳቸውን ተግባር ለማከናወን ከወላጆቻቸው ሲለዩ በሌሎች ውሳኔ በስህተት አቅጣጫ በቀላሉ ይመራሉ። የባሕርይ መረጋጋት የላቸውም። ተግባራዊ መሆን በሚችል ፍጥነትና ርቀት የራሳቸውን ውሳኔ እንዲከተሉ ተትተው ስለማያውቁ አእምሮዎቻቸው በተገቢ ሁኔታ አላደጉም አልጠነከሩምም። ለረዥም ጊዜ ፈጽሞ በወላጆቻቸው ቁጥጥር ሥር ስለነበሩ በእነርሱ ሙሉ በሙሉ ይደገፋሉ፤ ለእነርሱ ወላጆቻቸው አእምሮአቸና ውሳኔያቸው ናቸው።--3T 132, 133 (1872). {1MCP 283.1}1MCPAmh 230.3

    በኃይል ወይም በፍርሃት አማካይነት የመቆጣጠር ውጤቶች።--በእነርሱ ሀላፊነት ሥር ያሉ ልጆችን አእምሮና ፈቃድ ሙሉ በሙሉ እንደሚቆጣጠሩ በመኩራራት የሚናገሩ ወላጆችና መምህራን በኃይል ወይም በፍርሃት እንዲገዙ የተደረጉ ልጆችን የወደ ፊት ሕይወት ማየት ቢችሉ ኖሮ ጉራቸውን ያቆሙ ነበር። እነዚህ ልጆች በሕይወት በሚገጥሙአቸው ጠበቅ ባሉ ኃላፊነቶች ድርሻቸውን ለመወጣት ሙሉ በሙሉ ያልተዘጋጁ ናቸው። እነዚህ ወጣቶች ከወላጆቻቸውና ከመምህራኖቻቸው ቁጥጥር ሥር መሆናቸው ሲያበቃና ለራሳቸው እንዲያስቡና እንዲሰሩ በሚገደዱበት ጊዜ የተሳሳተ መንገድ መከተላቸውና ለፈተና ኃይል መሸነፋቸው እርግጠኛ ነው። በዚህ ሕይወትም የተሳካላቸው አይሆኑም፣ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውም ተመሳሳይ የሆኑ ጉድለቶች ይታዩባቸዋል። --3T 133, 134 (1872). {1MCP 283.2}1MCPAmh 230.4

    የሚያነቃቃና የሚያጠነክር እርምት (ቅጣት)።--ከቤትና ከትምህርት ቤት ቅጣት ባሻገር ሁሉም ጥብቅ የሆነውን የሕይወት ሥነ-ሥርዓት መጋፈጥ አለባቸው። ለእያንዳንዱ ልጅና ወጣት በግልጽ መሰጠት ያለበት ትምህርት ይህን እንዴት በጥበብ መጋፈጥ እንዳለበት ነው። እግዚአብሔር እኛን መውደዱና ለእኛ ደስታ እየሰራ መሆኑ እውነት ነው፣ ሕጎቹን ሁል ጊዜ ብንታዘዝ ኖሮ በፍጹም ስቃይን የማናይ መሆኑም እውነት ነው፤ በዚህ ዓለም ከኃጢአት የተነሣ ስቃይ፣ ችግር፣ ሸክሞች ወደ እያንዳንዱ ሕይወት መምጣታቸውም እውነት ነው። ልጆችና ወጣቶች እነዚህን ችግሮችና ሸክሞች በድፍረት እንዲጋፈጡ ስናስተምራቸው ለእድሜ ልክ የሚጠቅማቸውን መልካም ነገር እያደረግንላቸው ነው። ርኅራኄ ማሳየት የሚገባ ቢሆንም በሚገጥማቸው ነገር ከመጠን ያለፈ ደስታ የራቃቸው እንዲሆኑ የሚያደርጋቸው በፍጹም መሆን የለበትም። የሚያስፈልጋቸው ነገር የሚያነቃቃና የሚያጠነክር እንጂ የሚያደክም መሆን የለበትም። --Ed 295 (1903). {1MCP 283.3}1MCPAmh 231.1

    በብረት ለታጠሩ ሕጎች የተሰጠ አስተያየት።-- ሥነ-ሥርዓት በምታስተምሩበት ጊዜ ቅንጣት ያክል ጭካኔን አታስገቡ። በወጣቶች ላይ ግትር የሆኑ እገዳዎችን አትጣሉ። አንዳንድ ጊዜ ማድረግ የሌለባቸውን ነገሮች ማድረግ እንዳለባቸው እንዲሰማቸው የሚመሩአቸው እነዚህ በብረት የታጠሩ ደንቦችና ትዕዛዞች ናቸው። ወጣቶችን ስታስጠነቅቁ ወይም ስትገስጹ በእነርሱ ላይ የተለየ ፍላጎት እንዳለው ሰው አድርጉ። በሰማይ ባሉ መጻሕፍት መልካም ነገር እንዲጻፍላቸው ልባዊ የሆነ ፍላጎት እንዳላችሁ አሳዩአቸው። --Lt 67, 1902. (MM 180). {1MCP 284.1}1MCPAmh 231.2

    ለወጣቶች ሸክሞችን መሸከም ከባድ ነው።--ወጣቶች ትዕቢታቸውንና ራስ ወዳድነታቸውን በመተው ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ቀድሰው ቢሰጡ ኖሮ ኃይለኛ ተጽእኖ ማሳደር ይችሉ ነበር፤ ነገር ግን እንደ አጠቃላይ ነገር ሲታይ ለሌሎች ሸክሞችን አይሸከሙም። እራሳቸው የሚሸከማቸው ያስፈልጋቸዋል። በዚህ ረገድ እግዚአብሔር ለውጥን የሚፈልግበት ጊዜ መጥቶአል። ወጣቶችና አዛውንት ቀናተኞች እንዲሆኑና ንስሃ እንዲገቡ ይጠራቸዋል። በለብተኝነታቸው ቢቀጥሉ ከአፉ ይተፋቸዋል። እውነተኛው ምስክር ‹‹ሥራህን አውቃለሁ›› ይላል። ወጣት ወንዶችና ሴቶች ሆይ፣ ሥራችሁ ክፉ ወይም መልካም ቢሆን ይታወቃል። በመልካም ሥራ የበለጸጋችሁ ናችሁን? ኢየሱስ እንደ መካሪ ወደ እናንተ በመምጣት እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሀብታም እንድትሆን በእሳት የተፈተነውን ወርቅ፣ የራቁትነትህ ሀፍረት እንዳይገለጥ ትለብስ ዘንድ ነጭ ልብስ፣ ማየት እንድትችል ዓይንህን የምትኳልበትን የዓይን ኩል ከእኔ ትገዛ ዘንድ እመክርሃለሁ›› (ራዕይ 3፡ 18)። --1T 485 (1867). {1MCP 284.2}1MCPAmh 231.3

    ሀሳቦች ልማዶች ይሆናሉ።--የንጹህ ሀሳቦች የሚያከብር ኃይል ስሜት ያለማቋረጥ ሊሰማን ይገባል። ለማንኛውም ነፍስ ብቸኛው ደህንነት ትክክለኛ አስተሳሰብ ነው። ሰው ‹‹በልቡ እንደሚያስብ እንዲሁ ነውና›› (ምሳሌ 23፡ 7)። ራስን የመቆጣጠር ኃይል የሚጠነክረው በልምምድ ነው። በመጀመሪያ ከባድ የሚመስለው ነገር ያለ ማቋረጥ ሲደጋገም፣ ትክክለኛ የሆኑ ሀሳቦችና ተግባሮች የተለመዱ እስኪሆኑ ድረስ፣ እየቀለለ ይሄዳል። ፈቃደኛ ከሆንን ርካሽና ዝቅተኛ ከሆነ ነገር ሁሉ እንመለስና ከፍ ወዳለው መስፈርት እንነሳለን፤ በሰዎች የተከበርንና በእግዚአብሔር የተወደድን እንሆናለን። --MH 491 (1905). {1MCP 285.1}1MCPAmh 232.1

    ከታሪክ የተወሰዱ አሳዛኝ ምሳሌዎች።--የናፖሊዮን ቦናፓርቴ ባህርይ በከፍተኛ ደረጃ ተጽእኖ ያደረበት በልጅነቱ ጊዜ ባገኘው ስልጠና ነው። ጥበብ የሌላቸው መምህራን የወረራ ፍቅርን፣ የኩረጃ ሰራዊትን የመመስረትንና ራሱን የእነርሱ አዛዥ የማድረግን ፍቅር በውስጡ አነሳሱ። ለጦርነትና ደም ለማፍሰስ ሥራው መሰረት የተጣለው እዚህ ነበር። እርሱን ጥሩ ሰው ለማድረግ፣ የወጣትነት ልቡን በወንጌል መንፈስ ለመሙላት፣ ተመሳሳይ የሆነ ጥንቃቄና ጥረት ተደርጎ ቢሆን ኖሮ የእርሱ ታሪክ እንዴት ሰፊ ልዩነት ያለው ይሆን ነበር።{1MCP 285.2}1MCPAmh 232.2

    ሁሜ የተባለ ተጠራጣሪ ሰው በልጅነቱ ኃላፊነቱን በደንብ መወጣት የሚፈልግና በእግዚአብሔር ቃል የሚያምን ነበር። ከክርክር ማህበር ጋር ግንኙነት በመፍጠሩ አረመኔነትን (እምነት የለሽነትን) ደግፎ ክርክር እንዲያቀርብ ተመረጠ። በጽናትና በትዕግስት በማጥናቱ ንቁ የነበረው አእምሮው በጥርጣሬ ስህተት ተሞላ። ብዙም ሳይቆይ አታላይ ትምህርቶችን ስላመነ ከዚያ በኋላ የነበረው ሕይወቱ የአለማመንን ጥቁር አሻራ ተሸከመ። --ST, Oct 11, 1910. (CG 196.) {1MCP 285.3}1MCPAmh 232.3

    የማንበብ ተጽእኖ። [በምዕራፍ 13 ላይ ‹‹የአእምሮ ምግብ›› የሚለውን ይመልከቱ]።--ብዙ ወጣቶች ለመጻሕፍት ጉጉት አላቸው። ማግኘት የሚችሉትን ማንኛውንም ነገር ያነባሉ። ወላጆች እንደ እነዚህ ያሉ ልጆችን የማንበብ ፍላጎት እንዲቆጣጠሩ እማጸናቸዋለሁ። የፍቅር ታሪኮች ያሉባቸው መጽሔቶችና ጋዜጣዎች በጠረጴዛችሁ ላይ እንዲሆኑ አትፍቀዱ። በእነርሱ ቦታ ወጣቶች በባሕርይ ግንባታቸው ላይ እጅግ የተሻሉ ነገሮችን--እግዚአብሔርን መፍራትንና መውደድን፣ የክርስቶስን እውቀት-- እንዲያስቀምጡ የሚረዱ መጻሕፍት አስቀምጡ። ልጆቻችሁ በአእምሮአቸው ውስጥ ጠቃሚ የሆነ እውቀትን እንዲያከማቹ፣ ለወረዱና አዋራጅ ለሆኑ ሀሳቦች ቦታ እንዳይሰጡ፣ ጥሩ የሆነው ነገር ነፍስን እንዲይዝና ኃይሎቹን እንዲቆጣጠር እንዲፈቅዱ አደፋፍሩአቸው። ለአእምሮ ጥሩ ምግብ ለማይሰጥ የሚነበብ ነገር ያለውን ፍላጎት ገድቡ። ለታሪክ መጽሔቶች የሚወጣ ገንዘብ ብዙ አይመስልም፣ ነገር ግን ወደ ስህተት የሚመራ ብዙ ነገርን እና ትርፉ ጥሩ የሆነ ትንሽ ነገርን ለሚሰጡ መጻሕፍት የሚወጣ ገንዘብ እጅግ ብዙ ነው።--CT 133 (1913). {1MCP 285.4}1MCPAmh 232.4

    አእምሮ የሚመለከታቸውን ነገሮች ደረጃ ይይዛል።--አእምሮ ትውውቅ የሚፈጥርባቸውን ነገሮች ደረጃ ይወስዳል። ሁሉም መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ቢያጠኑ ኖሮ፣ [በምዕራፍ 11 ላይ ‹‹የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትና አእምሮ›› የሚለውን ይመልከቱ።]፣ በደንብ ያደጉ፣ የበለጠውን በጥልቀት ማሰብ የሚችሉ እና ተራ የዓለምን ሳይንሶችና ታሪኮች ለማጥናት የተደረጉ ልባዊ ጥረቶች አዋቂ ከሚያደርጉአቸው የበለጠ በከፍተኛ ደረጃ እውቀት ያላቸው ይሆኑ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ እውነተኛ ለሆነ ፈላጊ ያደገ የአእምሮ ትምህርትን ስለሚሰጥ መለኮታዊ ነገሮችን ከማሰላሰሉ የተነሣ የአእምሮ ኃይሎቹ ይበለጽጋሉ፤ እግዚአብሔርና የእርሱ የተገለጠ እውነት ከፍ ሲል ራስ ትሁት ይሆናል።-- RH, Aug 21, 1888. (FE 130.) {1MCP 286.1}1MCPAmh 233.1

    የግል ኃይማኖታዊ ልምምድ ዋጋ።--እግዚአብሔር የሀሳባችን ከፍተኛው ጉዳይ መሆን አለበት። እርሱን ማሰላሰልና መማጸን ነፍስን ከፍ ያደርጋል፣ የፍቅር ስሜትንም ይቀሰቅሳል። ማሰላሰልንና መጸለይን ችላ ማለት በርግጠኝነት የኃይማኖታዊ ፍላጎትን ማሽቆልቆል ያስከትላል። በዚያን ጊዜ ግድ የለሽነትና ስንፍና ይታያል። {1MCP 286.2}1MCPAmh 233.2

    ኃይማኖት ዝም ብሎ ስሜት አይደለም። ከሁሉም ዕለታዊ ተግባሮችና ልውውጦች ጋር የተጠላለፈ መርህ ነው። የዚህን መርህ አብሮ መሆን የሚከለክል ማንኛውም ነገር አይስተናገድም፣ ማንኛውም የንግድ ሥራ አይሰራም። ንጹህና ያልተበከለ ኃይማኖትን ለማቆየት በትዕግስት ጥረት የምናደርግ ሰራተኞች መሆን ያስፈልጋል። {1MCP 286.3}1MCPAmh 233.3

    ራሳችን የሆነ ነገር ማድረግ አለብን። የእኛን ሥራ ማንም ሊሰራልን አይችልም። መዳናችንን በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ መሥራት ያለብን እኛው ነን። ጌታ እንድንሰራው የተወልን ሥራ ይህ ነው። --2T 505, 506 (1870). {1MCP 287.1}1MCPAmh 233.4

    ወጣቶች የሥራ ሥነ-ሥርዓት ያስፈልጋቸዋል።--በእሥራኤል ዘመን እንደነበረው ሁሉ አሁንም እያንዳንዱ ወጣት የተግባራዊ ሕይወት ሥራዎችን መማር አለበት። አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ለሕይወት የሚያስፈልገውን ነገር ሰርቶ ማግኘት እንዲችል እያንዳንዱ ወጣት በሆነ የጉልበት ሥራ ዘርፍ እውቀት ማግኘት አለበት። ይህ የሚያስፈልገው ከሕይወት ውጣ ውረዶች ሊጠብቀን ብቻ ሳይሆን በአካል፣ በአእምሮና በግብረገብ እድገት ላይ ካለው ተጽእኖ ሊጠብቀንም ጭምር ነው። ግለሰቡ ራሱን ለመደገፍ በጉልበት ሥራ ላይ መሰማራት በፍጹም እንደማያስፈልግ እርግጠኛ ቢሆንም ሥራን መማር አለበት። ያለ አካል እንቅስቃሴ ማንም ቢሆን ጤናማ የሆነ አቋምና ብርታት ያለበት ጤንነት ሊኖረው አይችልም፤ በደንብ ቁጥጥር የተደረገበትን ስራ መማር ጠንካራና ንቁ አእምሮን እና የከበረ ባሕርይን ለማግኘት አስፈላጊነቱ አነስተኛ አይደለም። --PP 601 (1890). {1MCP 287.2}1MCPAmh 233.5

    ሥራ መፍታት ኃጢአት ነው።--ጠቃሚ የሆነ ሥራን ችላ ማለት የእውነተኛ ወንድ ወይም ሴት አስፈላጊ ባሕርይ ነው የሚለው አመለካከት እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ያቀደው እቅድ ተቃራኒ ነው። ሥራ መፍታት ኃጢአት ሲሆን ተራ የሆኑ ሥራዎችን አለማወቅ በኋለኛው ሕይወት መራር ለሆነ ጸጸት ሰፊ እድል የሚፈጥር ሞኝነት ነው። --ST, June 29, 1882. (FE 75.) {1MCP 287.3}1MCPAmh 234.1

    የቤት ውስጥ ሥራን ማሰልጠን ችላ መባል የለበትም።--በልጅነትና በወጣትነት ጊዜ የተግባርና የቀለም ትምህርት ሥልጠና ተደባልቆ መሰጠት አለበት። ልጆች በቤት ውስጥ ባሉ ሥራዎች ድርሻቸውን እንዲወጡ መማር አለባቸው። መስራት የሚችሉአቸውን ትንንሽ ነገሮች በመስራት አባትንና እናትን እንዴት እንደሚረዱ መማር አለባቸው። አእምሮዎቻቸው እንዲያስቡ፣ የማስታወስ ችሎታዎቻቸው የተመደበላቸውን ሥራ ለማስታወስ መሰልጠን አለባቸው፤ ጠቃሚ የሚያረጉአቸውን ልማዶች በቤት ውስጥ ሲሰለጥኑ ለእድሜያቸው ገጣሚ የሆኑ የተግባር ሥራዎችን እንዲሰሩ እየሰለጠኑ ናቸው። ልጆች ተገቢ የሆነ የቤት ሥልጠና ቢኖራቸው ኖሮ ብዙዎች እያገኙ ያሉትን ያልታቀደ ትምህርት በመውሰድ በጎዳናዎች ላይ አይገኙም ነበር። ልጆቻቸውን ምክንያታዊ በሆነ ሁኔታ የሚወዱ ወላጆች የስንፍና ልማዶችን ይዘው እንዲያድጉና የቤት ውስጥ ስራዎችን መስራት የማያውቁ ሆነው እንዲያድጉ አይፈቅዱም። --CT 149 (1913). {1MCP 287.4}1MCPAmh 234.2

    እያንዳንዷ ሴት ማወቅ የሚገባት ነገር።--በደንብ ተምረዋል የሚባሉ ብዙ ሴቶች፣ ከአንዳንድ የትምህርት ተቋማት በክብር ቢመረቁም በሚያሳፍር ሁኔታ ተግባራዊ ለሆኑ የህይወት ሥራዎች እውቀት የሌላቸው ናቸው። ቤተሰብን በተገቢ ሁኔታ ለመቆጣጠርና ለቤተሰብ ደስታ አስፈላጊ የሆኑ ብቃቶች የሉአቸውም። ስለ ሴቶች ከፍ ያለ የሥራ መስክና ስለ መብቶቻቸው ሊናገሩ ይችላሉ፣ ሆኖም ሴት መገኘት ከሚገባት እውነተኛ የሥራ መስክ እጅግ ወርደው ይገኛሉ። {1MCP 288.1}1MCPAmh 234.3

    እያንዳንዷ የሄዋን ልጅ የቤት ውስጥ ተግባራትን በደንብ የማወቅ፣ በቤት ውስጥ ሥራ በእያንዳንዱ ዘርፍ ስልጠና የማግኘት መብት አላት። እያንዳንዷ ወጣት ሴት የሚስትነትንና የእናትነትን ቦታ እንድትይዝ ብትጠራ በራሷ ግዛት እንደ ንግስት መምራት እንድትችል መማር አለባት። ልጆቿን ለመምራትና ለማስተማር ሙሉ በሙሉ ብቁ መሆን አለባት።... {1MCP 288.2}1MCPAmh 235.1

    ስለ ሰብአዊ አካል አሰራርና ስለ ንጽህና መርሆዎች፣ የአመጋገብና የአለባበስ ጉዳዮችን፣ ስለ ሥራና መዝናኛ፣ እንዲሁም የቤተሰቧን ደህንነት የሚመለከቱትን ሌሎች ቁጥር የለሽ ነገሮችን መረዳት መብቷ ነው። ልጆቿ ሲታመሙባት ውድ ሀብቶቿን እንግዳ በሆኑ ነርሶችና ሀኪሞች እጅ ከመተው ይልቅ በራሷ አቅም መፍትሄ ሊፈለግለት የሚችለውን በሽታን ማከም የሚቻልባቸውን የተሻሉ ዘዴዎችን በተመለከተ እውቀት ማግኘት መብቷ ነው። -- ST, June 29, 1882. (FE 75.) {1MCP 288.3}1MCPAmh 235.2

    ሴቶች አእምሮን ማሰልጠን ሲያቅታቸው።--በአጠቃላይ ሲታይ ራሷን የሰጠች ኃይማኖተኛ እንደሆነች የምትናገር ሴት አእምሮን ማሰልጠን ያቅታታል። አእምሯቸውን ወደ ፈለገበት እንዲሄድ ያለ አንዳች ቁጥጥር ስድ ይለቁታል። ይህ ትልቅ ስህተት ነው። ብዙዎች የአእምሮ ኃይል የሌላቸው ይመስላሉ። አእምሮ እንዲያስብ አላስተማሩትም፤ ይህን ስላላደረጉ ማድረግ እንደማይችሉ ይገምታሉ። በጸጋ ለማደግ ማሰላሰልና ጸሎት አስፈላጊ ናቸው። {1MCP 288.4}1MCPAmh 235.3

    በሴቶች መካከል መረጋጋት የሌለበት ምክንያት አእምሮአቸውን ስላላሰለጠኑና በጥልቀት ስለማያስቡ ነው። አእምሮ ያለ ሥራ እንዲቆይ በመተው ሌሎች የአእምሮ ሥራን እንዲሰሩ፣ እንዲያቅዱ፣ እንዲያስቡና እንዲያስታውሱላቸው ስለሚተዉ የበለጠውን ብቃት እያጡ ይሄዳሉ። አንዳንዶች አእምሮአቸውን በሥራ መግራት ያስፈልጋቸዋል። እንዲያስብ ማስገደድ አለባቸው። እንዲያስብላቸውና ችግሮቻቸውን እንዲፈተላቸው በሆነ ሰው ሲደገፉና አእምሮ በሀሳብ እንዳይጠመድ ሲያደርጉ ማስታወስ ያለመቻል፣ አሻግረው ወደ ፊት ማየት ያለመቻልና ነገሮችን መለየት ያለመቻል ችግር ይቀጥላል። እያንዳንዱ ግለሰብ አእምሮን ለማስተማር ጥረቶችን ማድረግ አለበት።-- 2T 187, 188 (1868). {1MCP 289.1}1MCPAmh 235.4

    ሴቶች የሚለብሱአቸው ልብሶች የአእምሮአቸው አመልካች ነው።--ልብስ የአእምሮና የልብ አመልካች ነው። በውጭ የሚንጠለጠለው በውስጥ ያለው ነገር ምልክት ነው። ከመጠን በላይ መልበስ የአእምሮ ችሎታን ወይም የሰለጠነ አእምሮን አይጠይቅም። ሴቶች በአካሎቻቸው ላይ ይህን ያህል ብዙ አስፈላጊ ያልሆኑ የልብስ ዓይነቶችን መልበስ የሚችሉበት ዋናው እውነታ የማሰብ ችሎታዎቻቸውን ለማሳደግና አእምሮአቸውን ጠቃሚ በሆነ እውቀት ለመሙላት ጊዜ ማግኘት ስለማይችሉ ነው።--MS 76, 1900. {1MCP 289.2}1MCPAmh 235.5

    በሀሳብና በተግባር ንጽህና ያስፈልጋል።--በእያንዳንዱ ሀሳብ፣ በእያንዳንዱ ቃል፣ በእያንዳንዱ ድርጊት ንጽህና እንዲኖር አደፋፍራለሁ። ለእግዚአብሔር በግላችን ተጠያቂዎች እንሆናለን፣ ማንም ሰው ሊሰራልን የማይችል የግላችን ሥራ አለ። እርሱም በቃላችን፣ በግል ጥረታችንና በሕይወት ምሳሌነታችን ዓለምን የተሻለ ማድረግ ነው። ማህበራዊነትን ማሳደግ ቢኖርብንም ለመደሰት ብቻ ሳይሆን ለዓላማ ይሁን። መዳን ያለባቸው ነፍሳት አሉ።--RH, Nov 10, 1885. (Ev 495.) {1MCP 289.3}1MCPAmh 236.1

    ሴጋ አእምሮን ያዋርዳል። [ ቻይልድ ጋይዳንስ የሚለውን መጽሐፍ ገጽ 439-468ን ይመልከቱ]--አንዳንድ ልጆች ራሳቸውን የመበከል ልምምድ የሚጀምሩት ገና በሕጻንነታቸው ነው፤ ዕድሜያቸው እየጨመረ ሲሄድ የፍትወተኛነት ስሜቶች ከእድገታቸው ጋር አብረው ያድጉና ከጥንካሬያቸው ጋር አብረው ይጠነክራሉ። አእምሮአቸው እረፍት የለውም። ወንዶች ከሴቶች ጋር መሆን፣ ሴቶችም ከወንዶች ጋር መሆን ይፈልጋሉ። ጠባያቸው ቁጥብነትና ጨዋነት የሌለው ነው። ደፋሮችና ግልጾች ስለሆኑ ጋጣወጥ የሆነ ነጻነትን ያሳያሉ። ራስን ያለ አግባብ የመጠቀም ልማድ አእምሮአቸውን አዋርዶአል፣ ነፍሶቻቸውንም አርክሶአል። መጥፎ ሀሳቦችን፣ ልበ-ወለዶችንና የፍቅር ታሪኮችን ማንበብ እና መጥፎ መጻሕፍት ሀሳባቸውን ይቀሰቅሱና ነውረኛ ከሆኑ አእምሮዎቻቸው ጋር ይስማማሉ። {1MCP 290.1}1MCPAmh 236.2

    ሥራን አይወዱም፣ ሥራ ሲሰሩ ደከመኝ ይላሉ፤ ጀርባቸውን ያማቸዋል፣ ራሳቸውን ያማቸዋል። ለዚህ በቂ መንስኤ የለውምን? ድካም የተሰማቸው ከሥራው የተነሣ ነውን? አይደለም፣ በፍጹም አይደለም! ሆኖም ወላጆች የልጆቻቸውን ማጉረምረም ይሰሙና ከሥራና ከሀላፊነት ነጻ ያደርጉአቸዋል። ይህ ለልጆቻቸው ከሚያደርጉላቸው ነገሮች እጅግ አስከፊው ነገር ነው። በዚህ ድርጊታቸው ሰይጣን ወደ ደከሙ አእምሮዎቻቸው በነጻነት እንዳይደርስ የሚከለክለውን ብቸኛ መለያ እያስወገዱ ነው። ጠቃሚ ሥራ በተወሰነ ደረጃ ሰይጣን በጽኑ እንዳይቆጣጠራቸው መጠበቂያ ይሆናል። --2T 481 (1870). {1MCP 290.2}1MCPAmh 236.3

    ወጣቶች ጉልበትን ይጠቀማሉ።--በደንብ የተደራጀና የሰለጠነ የወጣትነት መክሊት በቤተ ክርስቲያኖቻችን ይፈለጋል። ወጣቶች ሞልቶ እየፈሰሰ ባለው ጉልበታቸው የሆነ ነገር ማድረግ ይችላሉ። ይህ ጉልበት በትክክለኛ መስመር ካልተመራ በቀር የራሳቸውን መንፈሳዊነት ሊጎዳ በሚችል ሁኔታ ጥቅም ላይ ስለሚውል ከእነርሱ ጋር ግንኙነት ላላቸውም ጉዳት ያመጣል።--GW 211 (1915). {1MCP 290.3}1MCPAmh 236.4

    ወጣቶች እንቅስቃሴ ይፈልጋሉ።-- ወጣቶች በተፈጥሮ እንቅስቃሴ ስለሚፈልጉ በመማሪያ ክፍል ውስጥ ተወስነው ከቆዩ በኋላ ታፍኖ ለነበረው ጉልበታቸው መውጫ ካላገኙ እረፍት የለሽ ይሆናሉ፣ በሚደረግባቸው ቁጥጥርም ትዕግስት ስለሚያጡ እጅግ ብዙ ትምህርት ቤቶችንና ኮሌጆችን በሚያዋርዱና ከንቱ ሕይወት ውስጥ እንዲዘፈቁ በሚያደርጉ ባለጌና ከሰው የማይጠበቁ የአካል እንቅስቃሴዎች ላይ ይሰማራሉ። ከቤቶቻቸው ሲወጡ ምንም ክፋት የማያውቁ ብዙ ወጣቶች በትምህርት ቤት ውስጥ በሚኖራቸው ግንኙነት ይበላሻሉ።--ST, June 29, 1882, (FE 72.) {1MCP 290.4}1MCPAmh 237.1

    ለአስተያየት ምላሽ ስጡ።--ለልጆችና ለወጣቶች ብቻ ጠቃሚ የሆነ ማንኛውም መዝናኛ እነርሱ ለሌሎች ጠቃሚ እንዲሆኑ እንደሚያደርጋቸው ዓይነት ትልቅ በረከት መሆን አይችልም። ወጣቶች በተፈጥሮ ጉጉና ተጽእኖ ሊደረግባቸው የሚችሉ ስለሆኑ ለአስተያየቶች ምላሽ ለመስጠት ፈጣን ናቸው። መምህር ለተክሎች እድገት በሚያቅድበት ጊዜ የትምህርት ቤቱን ግቢና መማሪያ ክፍሎችን በማስዋብ ፍላጎታቸውን ለመቀስቀስ ይሞክር። ውጤቱ እጥፍ ጥቅም ያለው ይሆናል። ተማሪዎች ለማስዋብ የሚፈልጉት ነገር እንዲበላሽባቸው ወይም እንዲታወክባቸው አይፈልጉም። የታረመ ፍላጎት፣ የሥርዓት ፍቅር እና ለነገሮች የመጠንቀቅ ልማድ ይበረታታል፤ የተፈጠረው ሕብረት የመፍጠርና የመተባበር መንፈስ ለተማሪዎቹ የእድሜ ልክ በረከት ይሆናቸዋል። --Ed 212, 213 (1903). {1MCP 291.1}1MCPAmh 237.2

    አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔርን እንደ አፍቃሪ አባት አድርገው ማየት ያቅታቸዋል።--በአጠቃላይ ሲታይ ወጣቶች የምህረት ጊዜ ሲዘገይ፣ ውድ የሆኑ የአመክሮ ሰዓቶች አንድ ትልቅ የዓመት በዓል የሆነላቸው ይመስል በዚህ ዓለም እግዚአብሔር ያስቀመጣቸው ለራሳቸው ደስታና ቀጣይነት ባለው ሁኔታ የራሳቸውን ፍላጎት እንዲያሟሉ እንደሆነ አድርገው ይመለከታሉ። ሰይጣን በዓለማዊ መዝናኛዎች ደስታን እንዲያገኙና እነዚህ መዝናኛዎች ጉዳት የማያስከትሉ፣ ንጹህ እና ለጤንነትም ቢሆን ጠቃሚ እንደሆኑ ለማሳየት ጥረት በማድረግ ለራሳቸው ምክንያት እንዲሰጡ ለመምራት የተለየ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል። መንፈሳዊነትና ለእግዚአብሔር ራስን አሳልፎ መስጠት ጤናን እንደሚጎዳ አድርገው አንዳንድ ሀኪሞች አስተያየት ሰጥተዋል። ይህ አስተያየት ለነፍሳት ጠላት ይመቸዋል።--1T 501 (1867). {1MCP 291.2}1MCPAmh 237.3

    ሕመምተኛ የሆኑ አስተሳሰቦች እግዚአብሔርን በተሳሳተ ሁኔታ እንዲታይ ያደርጋሉ።--የክርስቶስን ኃይማኖት በትክክል የማይወክሉና የታመመ አስተሳሰብ ያላቸው ግለሰቦች አሉ፤ የዚህ ዓይነቶቹ ንጹህ የሆነ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ኃይማኖት የላቸውም። አንዳንዶች ስለ ኃጢአታቸው ዕድሜያቸውን በሙሉ ራሳቸውን ይገርፋሉ፤ ማየት የሚችሉት ነገር ቢኖር የተከፋ የፍትህ አምላክን ነው። ክርስቶስንና በደሙ አማካይነት የሚያድነውን የእርሱን ኃይል ማየት አይችሉም። ይህ ክፍል በአጠቃላይ የሚያካትተው ሚዛናዊ አእምሮ የሌላቸውን ሰዎች ነው። {1MCP 291.3}1MCPAmh 237.4

    ከወላጆቻቸው በተላለፈው በሽታና በወጣትነት ጊዜ ባገኙት የተሳሳተ ትምህርት አማካይነት የግብረገብ ክፍሎች እንዲታመሙ በማድረግና በሁሉም ነጥቦች ላይ ምክንያታዊ በሆነ ሁኔታ ማሰብና መስራት እንዳይችሉ በማድረግ የሰውነት አቋምንና አእምሮን የሚጎዱ የስህተት ልማዶችን እንዲያገኙ አድርጎአቸዋል። ሚዛናዊ የሆኑ አእምሮዎች የሉአቸውም። እግዚአብሔርን መምሰልና ጽድቅ ለጤና ጎጂ አይደሉም፣ ነገር ግን ለአካል ጤናና ለነፍስ ብርታት ናቸው። --1T 501, 502 (1867). {1MCP 292.1}1MCPAmh 238.1

    ራስን የመቆጣጠር አስፈላጊነት።--ሁል ጊዜ የምታደርጉትን ነገር በስሜት ሳይሆን በመርህ አድርጉ። ተፈጥሮአዊ ችኩልነታችሁን በየዋህነትና በጨዋነት አለዝቡ። ጥልቀት የሌለውና የማይረባ ነገርን አታድርጉ። ከከናፍሮቻችሁ የወረደ ቀልድ አይውጣ። ሀሳቦች እንኳን እንዲያምጹ መፍቀድ የለባችሁም። ቁጥጥር ሊደረግባቸውና ለክርስቶስ በመታዘዝ እንዲማረኩ መደረግ አለባቸው። ቅዱስ በሆኑ ነገሮች ላይ ይሁኑ። ያኔ በክርስቶስ ፀጋ አማካይነት ንጹህና እውነተኛ ይሆናሉ። --MH 491 (1905). {1MCP 292.2}1MCPAmh 238.2

    ስሜታዊነትህን ከሕይወት ማስወገድ።--አሁን በተማሪነት ሕይወት ውስጥ ነህ፤ አእምሮህ መንፈሳዊ በሆኑ ርዕሶች ላይ ይሁን። ስሜታዊነትን በሙሉ ከሕይወትህ አስወግድ። ለራስህ ንቁ የሆነ መመሪያ በመስጠት ራስን በቁጥጥርህ ሥር አድርግ። አሁን ያለኸው በባሕርይ መመስረቻ ወቅት ነው፤ ከፍ ያለና ቅዱስ ፍላጎትን የሚቀንስ፣ እግዚአብሔር የሰጠህን ሥራ ለመስራት እየተዘጋጀህ ሳለህ ብቃትህን የሚቀንስ ማንኛውም ነገር እንደማይረባ ወይም እንደ ተራ ነገር መታየት የለበትም። {1MCP 292.3}1MCPAmh 238.3

    ሁል ጊዜ በምታደርጉት ነገር ትህትናን ማሳየት አለባችሁ፣ ነገር ግን የአእምሮ ችሎታዎቻችሁ በተጣጣመ ሁኔታ እንዲገለጡና እንዲሻሻሉ መስፈርታችሁን ከፍ አድርጉ። እያንዳንዱን ስህተት ለማረም ቁርጠኛ ሁኑ። በውርስ የተገኙ ዝንባሌዎች ሊሸነፉ ይችላሉ--ፈጣን፣ ኃለኛ የሆኑ የቁጣ መገለጫዎች በክርስቶስ ጸጋ ሙሉ በሙሉ ተለውጠው ይሸነፋሉ። በግላችን በእግዚአብሔር የሥራ ቦታ ላይ እንዳለን አድርገን ማሰብ አለብን። --Lt 23, 1893. {1MCP 292.4}1MCPAmh 238.4

    ምክር የሚያስፈልግበትን ሁኔታ መጋፈጥ።--ልጆች ከወላጆቻቸውና ከመምህራኖቻቸው ውሳኔ ተለይተው በራሳቸው እንዲያስቡና እንዲሰሩ መተው የለባቸውም። ልጆች በልምድ የዳበረውን ውሳኔ እንዲያከብሩና በወላጆቻቸውና በመምህራኖቻቸው እንዲመሩ ትምህርት ሊሰጣቸው ይገባል። አእምሮዎቻቸው ከወላጆቻቸውና ከመምህራኖቻቸው አእምሮ ጋር ሕብረት እንዲፈጥሩና የእነርሱን ምክር መስማት ቅድሚያ የሚሰጠው እንደሆነ መማር አለባቸው። ከዚያ በኋላ ይመራቸው ከነበረው ከወላጆቻቸውና ከመምህራኖቻቸው እጅ ወጥተው ሲሄዱ ባሕርያቸው በንፋስ እንደሚወዛወዝ ቄጠማ አይሆንም። 3T 133 (1872). {1MCP 293.1}1MCPAmh 239.1

    የሚጠበቀው ከፍተኛው ስልጠና።--ጌታ እውቀታችንን ለሌሎች የማካፈል ዓላማን በአእምሮአችን አድርገን ማግኘት የምንችለውን እውቀት ሁሉ እንድናገኝ ይፈልጋል። ለእግዚአብሔር ለመስራት ወይም ለመናገር የት ወይም እንዴት እንደሚጠራ ማወቅ የሚችል ማንም የለም። ሰዎችን እንዴት ሊጠቀምባቸው እንደሚችል ማየት የሚችል ሰማያዊ አባታችን ብቻ ነው። ደካማ የሆነ እምነታችን ለይቶ ማወቅ የማይችላቸው መልካም ዕድሎች በፊታችን ናቸው። አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የእግዚአብሔርን ስም በሚያስከብርበት መንገድ የቃሉን እውነቶች እጅግ ከፍተኛ በሆኑ ምድራዊ ባለሥልጣናት ፊት ማቅረብ እንድንችል አእምሮዎቻችን መሰልጠን አለባቸው። ለእግዚአብሔር ለመስራት ራሳችንን በአእምሮ እውቀት ብቁ የማድረግ አንዲት አጋጣሚ እንኳን እንድታመልጠን መፍቀድ የለብንም።--COL 333, 334 (1900). {1MCP 293.2}1MCPAmh 239.2

    ሁል ጊዜ ዝግጁ የሆነ አእምሮ።--አእምሮ ዝግጁነቱን በፍጹም አያቋርጥም። ለመልካም ወይም ለመጥፎ ተጽእኖዎች ክፍት ነው። ሰዓሊ የሰውን ፊት በተወለወለ ብረት ላይ እንደሚያትም ሁሉ ሀሳቦችና አሻራዎችም በልጅ አእምሮ ውስጥ ይታተማሉ፤ እነዚህ አሻራዎች ከምድር ምድራዊ ወይም ግብረገባዊና ኃይማኖታዊ ቢሆኑ በፍጹም ሊጠፉ (ሊፋቁ) የማይችሉ ናቸው። {1MCP 293.3}1MCPAmh 239.3

    የማገናዘብ ችሎታ ሲነቃቃ፣ አእምሮ ለመቀበል በጣም ዝግጁ ስለሚሆን የመጀመሪያዎቹ ትምህርቶች እጅግ ጠቀሜታ ያላቸው ይሆናሉ። እነዚህ ትምህርቶች በባሕርይ ግንባታ ላይ ኃይለኛ የሆነ ተጽእኖ አላቸው። እነርሱ ትክክለኛ የሆነ አሻራ ቢኖራቸውና፣ ልጁ በእድሜ እየገፋ ሲሄድ፣ በትዕግስት ቢከታተላቸው ኖሮ ምድራዊውም ሆነ ዘላለማዊው መዳረሻ ለመልካም ይቀረጽ ነበር። ይህ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡-‹‹ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው፡- ባረጀ ጊዜም ከእርሱ ፈቀቅ አይልም›› ምሳሌ 22፡ 6)።--SpTEd 71, c1897. (CT 143.) {1MCP 293.4}1MCPAmh 239.4

    ወጣትነት የመልካም ዕድል ጊዜ ነው።--የወጣቶች ልብ አሁን በላዩ ቅርጽ ማውጣት እንደሚቻል ሰም ስለሆነ ክርስቲያናዊ ባህርይን እንዲያደንቁ ልትመሩአቸው ትችላላችሁ፤ ነገር ግን በጥቂት አመታት ውስጥ ሰሙ ወደ ዓለትነት ሊለወጥ ይችላል። --RH, Feb 21, 1878. (FE 51.) {1MCP 294.1}1MCPAmh 240.1

    የፍቅር ስሜቶች እጅግ አንገብጋቢ የሆኑት፣ የማስታወስ ችሎታ እጅግ ጥሩ የሆነው፣ እና ልብ ለመለኮታዊ አሻራዎች እጅግ ተጋላጭ የሆነው በወጣቶች ውስጥ ነው፤ አሁን ባለው የዓለም አመለካከትና ሊመጣ ባለው ላይ ትልቅ መሻሻሎችን እንዲያመጡ የአካልና የአእምሮ ኃይሎች ለሥራ መዘጋጀት ያለባቸው በወጣትነት ጊዜ ነው።--YI, Oct 25, 1894. (SD 78.) {1MCP 294.2}1MCPAmh 240.2

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents