Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

አእምሮ፣ባሕርይና ማንነት፣ክፍል 1

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ 35—አንድን ነገር በስሜት ሕዋሳት አማካይነት መገንዘብ የሚኖረው ተጽእኖ

    የምሁራዊና የመንፈሳዊ ዓለሞች ሕግ።--በመመልከት እንለወጣለን የሚለው አባባል የምሁራዊውም ሆነ የመንፈሳዊ ተፈጥሮ ሕግ ነው። አእምሮ እንዲያስብ ከተፈቀደለት ርዕሶች ጋር ቀስ በቀስ ይለማመዳል። ለመውደድና ለማምለክ ከተለማመደው ነገር ጋር ይዋሃዳል። --GC 555 (1888). {1MCP 331.1}1MCPAmh 269.2

    ከውኃ ጥፋት በፊት የነበሩትን ሰዎች ክፉን መመልከት አበላሻቸው።--ሰዎች እግዚአብሔር ክፋታቸውን መታገስ እስከማይችል ድረስ ክፉን በመመልከት በአምሳሉ ስለተለወጡ በውኃ ጥፋት ተጠራርገው ተወሰዱ።--SpTEd 44, May 11, 1896. (FE 422.) {1MCP 331.2}1MCPAmh 269.3

    ወደተሻለ ሁኔታ መለወጥ።--ወደ ኢየሱስ በመመልከት ስለ እግዚአብሔር ብሩህና የበለጠ ግልጽ የሆኑ እይታዎችን ስለምናገኝ በመመልከት እንለወጣለን። መልካምነትና ባልንጀሮቻችንን መውደድ ሳናስብ የምናደርገው ተፈጥሮአዊ ባህሪያችን ይሆናል። ከመለኮታዊ ባህርይ ጋር አብሮ የሚሄድ ባህርይ እናሳድጋለን። በእርሱ አምሳያ በማደግ እግዚአብሔርን የማወቅ ችሎታችንን እናሰፋለን። ከሰማያዊ ዓለም ጋር አብልጠን ሕብረት በፈጠርን ቁጥር የዘላለማዊነትን እውቀትና ጥበብ ብልጽግና ለመቀበል ያለማቋረጥ የሚጨምር ኃይል ይኖረናል። --COL 355 (1900). {1MCP 331.3}1MCPAmh 269.4

    ወደ ከፋ ሁኔታ መለወጥ።--በመመልከት እንለወጣለን። እግዚአብሔር የባህርዩን ፍጽምናና ቅድስና ለሰዎች የገለጠባቸው እነዚያ ቅዱስ ጥቅሶች ችላ ሲባሉና የሰዎች አእምሮዎች ወደ ሰብአዊ ትምህርቶችና ንድፈ ሀሳቦች መሳብን ተከትሎ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሕያው አምልኮ ማሽቆልቆል መከተሉ ምን ያስደንቃል። ጌታ እንዲህ ይላል፣ ‹‹የሕያው ውኃ ምንጭ የሆንኩትን እኔን ትተውኛልና፣ ለራሳቸውም ጉድጓዶችን፣ ውኃ መያዝ የማይችሉ ጎድጓዶችን ቆፈሩ›› (ኤርምያስ 2፡ 13)።--GC 478 (1911). {1MCP 332.1}1MCPAmh 270.1

    በመመልከት ሕይወት ተለውጦአል።--የእግዚአብሔር ቃል ለእግራችን መብራት ለመንገዳችንም ብርሃን ነው። ‹‹አንተን እንዳልበድል ቃልህን በልቤ ውስጥ ሰወርሁ (መዝሙር 119፡ 11)። አስቀድሞ በእግዚአብሔር ቃል የተያዘ ልብ ሰይጣን እንዳያገኘው ተመሽጎአል። ክርስቶስን የየዕለቱ ወዳጅና የሚታወቅ ጓደኛ የሚያደርጉ ሰዎች የማይታይ ዓለም ኃይሎች ሁሉ በዙሪያቸው እንዳሉ ይሰማቸውና ወደ ኢየሱስ በመመልከት እርሱን ወደ መምሰል ይለወጣሉ። በመመልከት ወደ መለኮታዊ ምሳሌ ይለወጣሉ፤ ባህርያቸው ይለሰልሳል፣ ይሞረዳል፣ ለሰማያዊ መንግስት ገጣሚ ለመሆን ይከብራል።--4T 616 (1881). {1MCP 332.2}1MCPAmh 270.2

    መርጦ መገንዘብ።--እግዚአብሔር መሰማት ያለበትን ነገር ሁሉ እንድንሰማና መታየት ያለበትን ነገር ሁሉ እንድናይ አይፈልግም። እንዳንሰማ ጆሮዎቻችንን መድፈንና እንዳናይ ዓይኖቻችንን መጨፈን ታላቅ በረከት ነው። ትልቁ ስጋት መሆን ያለበት ትኩረት ባለመስጠታችንና በግድ የለሽነታችን ከእጃችን እንዳያመልጡንና ሥራውን ከመስራት ይልቅ የምንረሳ አድማጮች እንዳንሆን የራሳችንን ጉድለቶች ለመለየት የጠራ እይታ ማግኘትና አስፈላጊ የሆነውን ተግሳጽና ትምህርት ሁሉ ለመያዝ ፈጣን ጆሮ ማግኘት ነው። --1T 707, 708 (1868). {1MCP 332.3}1MCPAmh 270.3

    የመገንዘብ ኃይሎችን በተጠንቀቅ ማቆየት።--በመማክርት ጉባኤ እንድትካፈል ተጠርተህ ከሆነ የመገንዘብ ኃይሎችህ መረጃዎችን ለመመዘን በተገቢ ሁኔታ ላይ ስለመሆናቸው ራስህን ጠይቅ። በተገቢ ሁኔታ ላይ ካልሆንክ፣ አእምሮህ ግራ ተጋብቶ ከሆነ፣ በስብሰባው ላይ ለመሳተፍ መብት የለህም። ነጭናጫ ነህን? ስሜትህ ጣፋጭና መዓዛ ያለው ነው ወይስ የጥድፊያ ውሳኔዎችን ወደማድረግ ሊመራህ የሚችል የተረበሸና ደስ የማይል ነው? ከሆነ ሰው ጋር መጣላት የምትፈልግ መስሎ ይሰማሃልን? እንደዚህ ከሆነ ወደ ስብሰባው አትሂድ፤ ከሄድክ በእርግጠኝነት እግዚአብሔርን ታዋርዳለህ። {1MCP 332.4}1MCPAmh 270.4

    መንፈስህ እስኪረጋጋና በተገቢ ሁኔታ ለመያዝ ቀላል እስኪሆን ድረስ መጥረቢያን ውሰድና እንጨትን በመቁረጥ ላይ ወይም በሌላ አካላዊ እንቅስቃሴ ላይ ተሰማራ። ጨጓራህ በአእምሮ ውስጥ መረበሽን እንደሚፈጥር ሁሉ ቃላቶችህም በስብሰባው ውስጥ ረብሻን ይፈጥራሉ። በተረበሹ የምግብ መፍጫ አካሎች ብዙዎች ከሚገነዘቡት በላይ ብዙ ችግር ይፈጠራል። --MS 62, 1900. (MM 295.) {1MCP 333.1}1MCPAmh 271.1

    ግንዛቤ በህሊና ቁጥጥር ሥር ባሉ አካላዊ ልማዶች ተጽእኖ ይደርስበታል።--የሰይጣንን ወጥመዶች ለመለየት የጠራ አእምሮ እንዲኖራቸው የሚፈልጉ ሰዎች አካላዊ ፍላጎቶቻቸው በአእምሮና በህሊና ቁጥጥር ሥር እንዲሆኑ ማድረግ አለባቸው። የክርስቲያን ባህርይን ፍጹም ለማድረግ የሞራልና ከፍ ያሉ የአእምሮ ኃይሎች ብርቱ ተግባር አስፈላጊ ነው። የአእምሮ ብርታት ወይም ድክመት በዚህ ዓለምና በመጨረሻ ድነት የሚኖረንን ጠቃሚነት በተመለከተ የሚጫወታ ሚና አለው።--RH, Sept 8, 1874. (MYP 236, 237.) {1MCP 333.2}1MCPAmh 271.2

    የአካል እንቅስቃሴ ግንዛቤን ያሻሽላል።--ጤናና ብርታት ባሉበት ሁኔታ እንዲጠበቁ ከተፈለገ አእምሮና ጡንቻ ተመጣጣኝ በሆነ ሁኔታ መስራት አለባቸው። እንዲህ ሲሆን ወጣቶች ወደ እግዚአብሔር ቃል ጥናት ጤናማ የሆነ ግንዛቤንና በደንብ ሚዛናዊ የሆኑ ነርቮችን ማምጣት ይችላሉ። የተሟላ አስተሳሰብ ይኖራቸዋል፣ ከቃሉ የመጡላቸውን ውድ ነገሮችንም ይዘው ማቆየት ይችላሉ። እውነቶቹን በደንብ ስለሚቀስሙ እውነት ምን እንደሆነ ለይቶ የሚያውቅ የአእምሮ ኃይል ይኖራቸዋል። ያኔ፣ ሁኔታው እንደሚፈቅደው፣ በእነርሱ ስላለው ተስፋ ለሚጠይቃቸው ለእያንዳንዱ ሰው በየዋህነትና በፍርሃት መልስ መስጠት ይችላሉ።-- 6T 180 (1900). {1MCP 333.3}1MCPAmh 271.3

    ፍጽምናን መጨመር ግንዛቤን ይጨምራል።--ሰው ወደ ግብረገብ ፍጽምና እየቀረበ በሄደ ቁጥር፣ ስሜቶቹ ንቁ፣ ኃጢአትን ለይቶ የማወቅ ችሎታው ትክክለኛ እና በመከራ ውስጥ ላሉት የሚኖረው ርኅራኄ ጥልቅ ይሆናል።-- GC 570 (1911). {1MCP 333.4}1MCPAmh 271.4

    ሀዘን የማርያምን ግንዛቤ አደበዘዘው።--የኢየሱስን አካል ማን እንደወሰደው የሚነግራትን የሆነ ሰው አገኛለሁ ብላ እያሰበች ከእግዚአብሔር መላእክት እንኳን ፊቷን አዞረች። በዚህ ሰዓት ሌላ ድምጽ ‹‹አንቺ ሴት ለምን ታለቅሺያለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ?›› ብሎ አናገራት። እንባ ባፈዘዛቸው ዓይኖቿ ማሪያም የሰውን መልክ አየችና አትክልተኛ እንደሆነ በማሰብ እንዲህ አለች፣ ‹‹ጌታዬ፣ ከዚህ ወስደህ ከሆነ የት እንዳስቀመጥከው ንገረኝ፣ እኔ እወስደዋለሁ።›› --DA 790 (1898). {1MCP 334.1}1MCPAmh 271.5

    ኢየሱስን በድምጹ ለየች።--ነገር ግን ኢየሱስ በሚታወቀው በራሱ ድምጽ ‹‹ማሪያም›› ብሎ ጠራት። አሁን እያናገራት ያለው የማታውቀው ሰው እንዳልሆነ አወቀችና ዞር ስትል በፊቷ ሕያው ክርስቶስን ተመለከተች። ከደስታዋ የተነሣ መሰቀሉንም ረሳች። ወደ እርሱ በመሮጥ፣ እግሩን እንደመያዝ እያለች ‹‹መምህር›› አለች። --DA 790 (1898). {1MCP 334.2}1MCPAmh 272.1

    የምግብ ፍላጎት የመገንዘብ ኃይሎችን ሙት ሊያደርግ ይችላል።--የምግብ ፍላጎትን ያለ አግባብ ማርካት የአካል ድክመትን እያመጣ እንደነበርና ቅዱስና ዘላለማዊ ነገሮች ተለይተው እንዳይታወቁ የመገንዘብ ኃይሎችን እየገደለ እንደነበር የዓለም አዳኝ አወቀ። የራስን ፍላጎት ማሟላት የግብረገብ ኃሎችን እያዛባ እንደሆነ እና ለሰው የሚያስፈልገው ትልቁ ነገር መለወጥ እንደሆነ አወቀ። ያ ለውጥ ራስን ከማስደሰት ሕይወት ራስን ወደ መካድና ራስን መስዋዕት ወደ ማድረግ ሕይወት የሚያደርስ የልብ፣ የአእምሮና የነፍስ ለውጥ ነው። --Lt 158, 1909. (MM 264.) {1MCP 334.3}1MCPAmh 272.2

    ኃጢአት ግንዛቤን ያደበዝዛል።--አእምሮዎቻችንን የሚያጨልምና ግንዛቤዎቻችንን የሚያደበዝዝ ኃጢአት ነው። ኃጢአት ከልባችን ሲወገድ በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት የእግዚአብሔርን ክብር የማወቅ ብርሃን፣ ቃሉን እያበራ እና ከተፈጥሮ ፊት በመንጸባረቅ እንዲህ በማለት እርሱን በሙላት ያውጃል፡- ‹‹መሃሪ፣ ሞገስ ያለው ታጋሽም፣ ባለ ብዙ ቸርነነትና እውነት›› (ዘጸአት 34፡ 6)። {1MCP 334.4}1MCPAmh 272.3

    አእምሮ፣ ልብና ነፍስ ወደ እርሱ ቅድስና ምስል እስኪለወጡ ድረስ በእርሱ ብርሃን ብርሃንን እናያለን።-- MH 464, 465 (1905). {1MCP 335.1}1MCPAmh 272.4

    የግንዛቤ ኃይሎች ሲጨልሙ።--ኩራት፣ የራስ ፍቅር፣ ራስ ወዳድነት፣ ጥላቻ፣ ቅንዓት እና ምቀኝነት የመገንዘብ ኃይሎችን አጨልመዋል።--2T 605 (1871). {1MCP 335.2}1MCPAmh 272.5

    ክርስቶስ በኃጢአት የደነዙ ግንዛቤዎችን እንዴት እንደተገናኘ።--ክርስቶስ ወደ ወደቀው ሰብአዊ ዘር በመድረስ ወደ ላይ ለማንሳት በራሱ ላይ ሰብአዊ ተፈጥሮን ለመቀበል ዝቅ አለ። ነገር ግን ሰዎች ከሰብአዊነት ልብስ ሥር ያለውን የእርሱን መለኮታዊ ባህርይ መለየት እንዳይችሉ አእምሮዎቻቸው በኃጢአት ጨልመዋል፣ ችሎታዎቻቸው ደንዝዘዋል፣ ግንዛቤዎቻቸውም ደብዝዘዋል። ይህ በእነርሱ በኩል የአድናቆት መጥፋት እርሱ ለእነርሱ መስራት ለሚፈልገው ሥራ እንቅፋት ነው፤ ብዙ ጊዜ ለትምህርቱ ኃይል ለመስጠት አቋሙን መግለጽና መከላከል አስፈላጊ እንደሆነ ይሰማው ነበር። {1MCP 335.3}1MCPAmh 272.6

    ምስጢራዊና መለኮታዊ ባህርዩን በመጥቀስ አእምሮዎቻቸውን ለእውነት የመለወጥ ኃይል ምቹ ሊያደርግ ወደሚችል ሀሳብ ለመምራት አሰበ። እንዲሁም መለኮታዊ እውነትን ለማስረዳት እነርሱ የሚያውቁአቸውን በተፈጥሮ ውስጥ ያሉ ነገሮችን ተጠቀመ። መልካሙን ዘር ለመቀበል የልብ መሬት በዚህ መልክ ተዘጋጅቶ ነበር። አድማጮቹ የእርሱ ፍላጎት ከእነርሱ ፍላጎት ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ፣ በደስታቸውም ሆነ በሀዘናቸው የእርሱ ልብ ከእነርሱ ልብ ጋር በርኅራኄ እየመታ እንደሆነ እንዲሰማቸው አደረገ። በተመሳሳይ ጊዜ እጅግ የተከበሩ መምህሮቻቸው ካላቸው እጅግ የበለጠ ኃይልና ልቀት መገለጥ በእርሱ ውስጥ አዩ። {1MCP 335.4}1MCPAmh 273.1

    የክርስቶስ ትምህርቶች ከዚህ በፊት በማያውቁት ትህትና፣ ስብዕና እና ኃይል የሚታወቁ ስለነበሩ ሳያስቡት እንዲህ በማለት ጮሁ፡- ‹‹ማንም ሰው እንደዚህ ሰው ተናግሮ አያውቅም።›› ሰዎች በደስታ አዳመጡት። --5T 746, 747 (1889). {1MCP 335.5}1MCPAmh 273.2

    ቁጥጥር ያልተደረገባቸው የፍቅር ስሜቶች የመገንዘብ ኃይሎችን ይጎዳሉ።--ዝቅተኞቹ ስሜቶች በጥብቅ መጠበቅ አለባቸው። ስሜቶች እንዲያምጹ ሲፈቀድላቸው የመገንዘብ ኃይሎች ያለ አግባብ ጥቅም ላይ ይውላሉ፣ አስከፊ በሆነ ሁኔታ ከአግባብ ውጭ ጥቅም ላይ ይውላሉ። ስሜቶች ከአግባብ ውጭ ሲፈጸሙ ደም ወደ ሁሉም የሰውነት ክፍሎች በመዘዋወር የልብ ጫናን ከመቀነስና አእምሮን ከማጥራት ይልቅ ተገቢ ከሆነ መጠን በላይ ወደ ውስጠኞቹ የአካል ክፍሎች ይሄዳል። ከዚህ የተነሣ በሽታ ይከሰታል። ክፉው ታይቶ መፍትሄ እስኪሰጠው ድረስ ግለሰቡ ጤናማ መሆን አይችልም። --SpT Series B, No. 15, p 18, Apr 3, 1900. (CH 587.) {1MCP 335.6}1MCPAmh 273.3

    አእምሮ ኃጢአትን እንዲቀበል ማስተማር ይቻላል።--ክርስቲያን ግልጽ የሆነ ኃጢአት ከመስራቱ በፊት፣ ዓለም ሳያውቅ፣ በልብ ውስጥ ረዥም የዝግጅት ጊዜ ይወስዳል። አእምሮ ከንጽህናና ከቅድስና በአንድ ጊዜ ወደ ህገወጥነት፣ ወደ ብልሽትና ወደ ወንጀል አይወርድም። በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠሩትን ወደ አረመኔነት ወይም ሳይጣናዊነት ማውረድ ጊዜ ይወስዳል። በመመልከት እንለወጣለን። ሰው ንጹህ ያልሆኑ ሀሳቦችን በማስተናገድ በአንድ ወቅት ይጸየፈው የነበረው ኃጢአት አስደሳች እንዲሆንለት ራሱን ማስተማር ይችላል። --PP 459 (1890). {1MCP 336.1}1MCPAmh 273.4

    የአካል ኃይሎች የጠላት መጫወቻ ይሆናሉ።--ሰው የተፈጥሮ አካሉን ሕግ እንዲጥስ እግዚአብሔር ፈቃድ አይሰጥም። ነገር ግን ሰው መሻትን አለመግዛትን ለመፈጸም ለሰይጣን ፈተናዎች በመሸነፍ ከፍ ያሉ የአካል ክፍሎችን እንስሳዊ ለሆነ የምግብ ፍላጎትና ስሜት ተገዥ ያደርጋል። እነዚህ ነገሮች የበላይነትን ሲያገኙ ከፍተኛ ለሆነ እድገት ተጋላጭ ከሆኑ የአካል ክፍሎች ጋር ከመላእክት ጥቂት አንሶ የተፈጠረው ሰው ሰይጣን እንዲቆጣጠረው እጁን ይሰጣል። በምግብ ፍላጎት ባርነት ሥር ካሉት ጋር በቀላሉ ግንኙነት ይፈጥራል። መሻታቸውን ካለመግዛታቸው የተነሳ ከአካል፣ ከአእምሮና ከግብረገብ ኃይሎቻቸው መካከል አንዳንዶች ግማሹን ሌሎች ደግሞ ሁለት ሶስተኛውን መስዋዕት በማድረግ ለጠላት መጫወቻ ይሆናሉ።--RH, Sept 8, 1874. (MYP 236.) {1MCP 336.2}1MCPAmh 274.1

    ጉዳት ሳይኖር ጉዳት እንዳለ ለገመተ ሰው የተሰጠ ምክር።--እህት ዲ በአንዳንድ ነገሮች ላይ ተታላለች። እግዚአብሔር በተለየ ሁኔታ መመሪያ እንደሰጣት ስላሰበች ሁለታችሁም አምናችሁ እሷ እንዳለችው አድርጋችኋል። በተለየ መልኩ ነገሮችን የመለየት ችሎታ እንዳላት ያሰበችው ነገር የጠላት ማታለያ ነው። እሷ በተፈጥሮዋ ለማየት ፈጣን፣ ለመረዳት ፈጣን፣ ለመገመት ፈጣን እና በተፈጥሮዋም እጅግ በጣም የሚሰማት ሴት ነች። ሰይጣን እነዚህን ባሕርያት እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ሁለታችሁንም በተሳሳተ መንገድ መርቶአችኋል። {1MCP 336.3}1MCPAmh 274.2

    ወንድም ዲ ሆይ፣ ረዘም ላለ ጊዜ ባሪያ ነበርክ። እህት ዲ መረዳት ብላ ትናገር ከነበረችው ነገር መካከል አብዛኛው ምቀኝነት ነበር። ሁሉንም ነገር በምቀኝነት ዓይን ለማየት፣ ተጠራጣሪ ለመሆን፣ ክፋትን ለማነሳሳት፣ ሁሉንም ነገር ላለማመን የተጋለጠች ነበረች። ይህ እምነትና መተማመን መኖር ባለበት ቦታ አእምሮ ደስተኛ እንዳይሆን፣ ሀዘንና ጥርጣሬ እንዲኖር ያደርጋል። ምንም እንኳን የሌሉ ነገሮች ቢሆኑም በቀላሉ የሚነካው ባህርይዋ ችላ እንደተባለች፣ እንደተቃለለችና እንደተጎዳች እንድታስብ ሲመሩአት ክፉ ነገር ይከሰታል ብላ የምታስብባቸው እነዚህ ደስተኛ ያልሆኑ ባህርያት ሀሳቦቿን ጨለምለም ወዳለ መስመር ይመልሳሉ።... {1MCP 337.1}1MCPAmh 274.3

    እነዚህ ደስታ የሌላቸው ባህርያት ጠንካራ በሆነ ፈቃድ መታረምና መታደስ አለባቸው፤ እንዲህ ካልሆነ ሁለታችሁም በመጨረሻ የእምነት ክስረት እንዲደርስባችሁ ያደርጋሉ። -- 1T 708, 709 (1868). {1MCP 337.2}1MCPAmh 274.4

    የሰይጣንን ኃይል አታጉላ።--የምንለወጠው በመመልከት ነው። በአምላካችንና በአዳኛችን ፍቅር ላይ ትኩረት ስናደርግ፣ በመለኮት ባህርይ ፍጽምና ላይ በማሰላሰልና የክርስቶስ ጽድቅ በእምነት የእኛ እንደሆነ በመናገር ወደ እርሱ አምሳል እንለወጣለን። ስለዚህ ደስ የማይሉ ስዕሎችን ሁሉ--የሰይጣን ኃይል ማስረጃዎች የሆኑትን በደሎችን፣ ኃጢአቶችንና ተስፋ መቁረጦችን--በአእምሮአችን አዳራሾች ላይ ለመስቀል፣ ነፍሶቻችን በተስፋ መቁረጥ እስኪሞሉ ድረስ ስለ እነርሱ ለመናገርና ለማዘን አንሰብስባቸው። ተስፋ የቆረጠ ነፍስ የእግዚአብሔርን ብርሃን እንዳይቀበል ራሱን ብቻ የሚከለክል ሳይሆን ሌሎችም እንዳያገኙ ስለሚዘጋ የጨለማ አካል ነው። ሰይጣን ሰብአዊ ፍጡሮችን እምነት የሌላቸውና ተስፋ የቆረጡ እንዲሆኑ በማድረግ የድሎቹን ምስሎች ውጤት ማየት ይወዳል። --5T 744, 745 (1889). {1MCP 337.3}1MCPAmh 274.5

    አከባቢ ተጽእኖ ያደርጋል።--ሕመምተኛ በብዛት ከቤት ውጭ እንዲቆይ ሲደረግ የሚፈልገው እንክብካቤ አነስተኛ ይሆናል። ዙሪያው አስደሳች ከሆነ እርሱም የበለጠውን ተስፋ ያለው ይሆናል። ቤቱ ምንም ያህል ውብ ቢሆን እቤት ውስጥ ከተዘጋ ደስተኛ ያልሆነና የሚተክዝ ይሆናል። በተፈጥሮ ውብ ነገሮች ከከበባችሁት፣ እያደጉ ያሉ አበቦችን ማየት በሚችልበትና ወፎች ሲዘምሩ በሚሰማበት ቦታ ብታስቀምጡት ከወፎች ዝማሬ ጋር በተጣጣመ ሁኔታ ልቡ ዝማሬን ያፈልቃል። እረፍት ወደ አካልና አእምሮ ይመጣል። አእምሮ ይነቃል፣ የማሰብ ችሎታ ይቀሰቀሳል፣ አእምሮም የእግዚአብሔርን ቃል ውበት ለማድነቅ ይዘጋጃል።--MH 265 (1905). {1MCP 338.1}1MCPAmh 275.1

    በአካባቢ ያሉ ነገሮች በልምምድ ላይ ተጽእኖ ያሳድራሉ።--ከዚያ በኋላ ከእግዚአብሔር ተለይታ በጨለማ የተከበበችን ትንሽ ልጃገረድ እንዳይ ተደረግሁ… መልአኩ እንዲህ አለ፡- ‹‹ለተወሰነ ጊዜ በጥሩ ሁኔታ ስትንቀሳቀስ ነበረች፤ በዚያው ሁኔታ እንዳትቀጥል የከለከላት ነገር ምን ነበር? ወደ ኋላ ጠቆመኝና ለውጡን ያመጣው የአካባቢ ለውጥ እንደሆነ አየሁ። ልክ እንደ እርሷ ካሉ በሳቅና በደስታ፣ በኩራትና በዓለም ፍቅር ከተሞሉ ወጣቶች ጋር ግንኙነት እየፈጠረች ነበር። ለክርስቶስ ቃላት ቦታ ሰጥታ ቢሆን ኖሮ ለጠላት አትሸነፍም ነበር። ‹‹ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ።›› በዙሪያችን ሁሉ ፈተና ሊኖር ይችላል፣ ነገር ግን ይህ ወደ ፈተና እንድንገባ አያደርገንም። እውነት ከሁሉም በላይ ነው። የእርሱ ተጽእኖ ዝቅ ወደ ማድረግ ሳይሆን ከፍ ወደ ማድረግ፣ ወደ መሞረድ፣ ወደ ማንጻትና ወደ ዘላለማዊነትና ወደ እግዚአብሔር ዙፋን ከፍ ወደ ማድረግ ያዘነብላል። መልአኩ እንዲህ አለ፣ ‹‹ክርስቶስን ወይስ ዓለምን ትመርጣላችሁ?›› {1MCP 338.2}1MCPAmh 275.2

    ሰይጣን ምሰኪን ለሆኑ ሟቾች ዓለምን እጅግ አታላይ በሆነና በሚያባብል ውበት ስለሚያቀርብ የዚያ ማብረቅረቅና ውበት የሰማይን ክብርና ልክ እንደ እግዚአብሔር ዙፋን ጸንቶ የሚኖረውን ሕይወት ይጋርዳል። ሀዘንን፣ ትካዜን፣ ስቃይን ወይም ሞትን የማያውቅ፣ ሰላም፣ ደስታና የማይነገር ፍስሃ የሞላበት ሕይወት በኃጢአት ለሚኖሩት አጭር ሕይወት መስዋዕት ተደርጓል። --2T 100, 101 (1868). {1MCP 338.3}1MCPAmh 275.3

    ማየት ማንነትን ይቀርጻል።--ዓይኖቿ የሚያዩአቸውና ጆሮቿ የሚሰሙአቸው ነገሮች ልቧን አዛብቶአል።-- 4T 108 (1876). {1MCP 338.4}1MCPAmh 276.1

    ጊዜያዊ ጥቅሞችን በመምረጥ ግንዛቤዎች ተወዛግበዋል።--ሎጥ እርሱንና ቤተሰቡን የሚከቡትን የግብረገብ ተጽእኖዎች ከመመልከት ይልቅ ሊያገኝ የሚችላቸውን ጊዜያዊ ጥቅሞች ስለተመለከተ ሶዶምን የመኖሪያ ቦታው አድርጎ መረጠ። የዚህ ዓለም ነገሮችን በተመለከተ ምን ትርፍ አገኘ? ንብረቶቹ ወድመዋል፣ ኃጢአተኛዋ ከተማ ስትጠፋ ከልጆቹ መካክል ግማሾቹ አብረው ጠፍተዋል፣ ሚስቱ በመንገድ ላይ ወደ ጨው አምድነት ተለውጣለች፣ እርሱ ራሱም የዳነው ‹‹በእሳት እንደዳነ›› ሆኖ ነበር። የራስ ወዳድነት ምርጫው ያስከተላቸው ክፉ ውጤቶች እዚህ አላቆሙም ነበር፤ የዚያ ቦታ የግብረገብ ብልሽት ከልጆቹ ባህርይ ጋር እጅግ የተጠላለፈ ከመሆኑ የተነሣ በመልካምና በክፉ፣ በኃጢአትና በጽድቅ መካከል ያለውን ልዩነት ማወቅ አልቻሉም ነበር። --ST, May 29, 1884. (MYP 419.) {1MCP 339.1}1MCPAmh 276.2

    ለዘላለማዊ እውነቶች የጨለሙ ግንዛቤዎች።--ለእግዚአብሔር ተቀድሶ የተለየውን ገንዘብ በተሳሳተ መንገድ ጥቅም ላይ ያዋሉ ሰዎች ስለ መጋቢነታቸው መልስ መስጠት ይጠበቅባቸዋል። አንዳንዶች ትርፍ ለማግኘት ካላቸው ፍቅር የተነሣ ገንዘቡን በራስ ወዳድነት ወስደዋል። ለሌሎች ገር የሆነ ህሊና የላቸውም፤ ለረዥም ጊዜ ሲንከባከቡ ከቆዩት ራስ ወዳድነት የተነሣ ጠቦአል።. . . {1MCP 339.2}1MCPAmh 276.3

    አእምሮዎቻቸው ለረዥም ጊዜ በወረደና ራስ ወዳድ በሆነ መስመር ሲንቀሳቀሱ ስለቆዩ ዘላለማዊ የሆኑ ነገሮችን ማድነቅ አይችሉም። ለድነት ዋጋ አይሰጡም። የድነትን ዕቅድ ወይም የስርየትን ዋጋ በትክክል መገመት እንዲችሉ አእምሮአቸውን ማንሳት የማይቻል ይመስላል። የራስ ወዳድነት ፍላጎቶች መላው አካል እንዲመሰጥ አድርገዋል፤ ዝቅ ካለው ደረጃ ጋር በማስተሳሰር ማግኔትነት እንዳለው ብረት አእምሮንና ስሜቶችን ይይዛሉ። ከእነዚህ ግለሰቦች መካከል አንዳንዶቹ የዚህን ዓይነት ባሕርይ ዋጋና አስፈላጊነት ስለማይመለከቱ የክርስቲያን ባሕርይ ፍጽምና ደረጃን በፍጹም መድረስ አይችሉም። ቅድስና እንዲያስደስታቸው አእምሮዎቻቸው ወደ ላይ ከፍ ማለት አይችሉም። የራስ ፍቅርና የራስ ወዳድነት ፍላጎቶች ባህርይን እጅግ ከማጣመማቸው የተነሣ ቅዱስና ዘላለማዊ የሆነውን ነገር ተራ ከሆነ ነገር መለየት እንዲችሉ ማድረግ አይቻልም። --2T 519, 520 (1870). {1MCP 339.3}1MCPAmh 276.4

    ግንዛቤን የሚቀሰቅስ ነገር።--ልቦች ከራስ ወዳድነትና ስለ ራስ ብቻ ከመለፍለፍ ሲነጹ እግዚአብሔር ከሚልክላቸው መልእክት ጋር የተጣጣሙ ይሆናሉ። ግንዛቤዎች ይቀሰቀሳሉ፣ ስሜቶችም የተሞረዱ ይሆናሉ። ተመሳሳይ ተመሳሳዩን ያደንቃል። ‹‹ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል›› (ዮሐንስ 8፡ 47)። --5T 696 (1889). {1MCP 339.4}1MCPAmh 277.1

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents