Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

አእምሮ፣ባሕርይና ማንነት፣ክፍል 1

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ 8—ኃይማኖትና አእምሮ

    [ምዕራፍ 43:- ‹‹አእምሮና መንፈሳዊ ጤንነት›› የሚለውን ይመልከቱ]

    የክርስቶስ ፍቅር ለመላው አካል ብርታትና ጉልበት ይሰጣል።--ክርስቶስ በመላው አካል ውስጥ እንዲሰርጽ የሚያደርገው ፍቅር ብርታት የመስጠት ኃይል አለው። እያንዳንዱን ለሕይወት አስፈላጊ ክፍል--አእምሮን፣ ልብን፣ ነርቮችን--በፈውስ ይነካል። በእርሱ አማካይነት የፍጡር ከፍተኛ ኃይላት ለተግባር ይነሳሳሉ። የነፍስን ኃይሎች ከሚደፈጥጡ ከበደለኝነትና ከሀዘን፣ ከሥጋትና ከጭንቀት ነጻ ያወጣል። እርሱ ሰላምንና መረጋጋትን ያመጣል። በነፍስ ውስጥ ምድራዊ የሆነ ምንም ነገር ሊያጠፋው የማይችለውን ደስታ ይተክላል፤ ያውም በመንፈስ ቅዱስ ደስታን፣ ጤና እና ሕይወት ሰጭ ደስታን ይሰጣል። --MH 115 (1905). {1MCP 65.1}1MCPAmh 55.1

    የክርስቶስ ሥራ ልባቸው የተሰበረውን መፈወስ ነው።--የእግዚአብሔር ፈዋሽ ኃይል በፍጥረት ሁሉ ውስጥ ያልፋል። ዛፍ ቢቆረጥ፣ ሰብአዊ ፍጡር ቢቆስል ወይም አጥንቱ ቢሰበር፣ ተፈጥሮ ወዲያውኑ የቆሰለውን አካል የመጠገን ሥራዋን ትጀምራለች። ችግሩ ከመፈጠሩ በፊት እንኳን የፈውስ ወኪሎች ሁል ጊዜ ዝግጁ ናቸው፤ የአካል አንዱ ክፍል ሲቆስል እያንዳንዱ የሰውነት አቅም ያን ቦታ ወደ ቀድሞ ሁኔታ የመመለስ ተግባር ላይ ይሰማራል። በመንፈሳዊው ዓለምም እንደዚሁ ነው። ኃጢአት ችግሩን ከመፍጠሩ በፊት እግዚአብሔር መፍትሄውን አስቀምጦአል። እያንዳንዱ ለፈተና የሚሸነፍ ነፍስ በጠላት ጥቃት ቆስሎአል፣ ተቀጥቅጦአል፤ ነገር ግን ኃጢአት ባለበት ሁሉ አዳኝ አለ። ‹‹ልባቸው የተሰበረውን መፈወስ፣ ለተጋዙት መፈታትን መስበክ፣…የተጨቆኑትን ነጻ ማውጣት›› (ሉቃስ 4፡ 18) የክርስቶስ ሥራ ነው። Ed 113 (1903). {1MCP 65.2}1MCPAmh 55.2

    ለአእምሮና ለመንፈሳዊ ሕመሞች አዳኙ የሚያዘው መድሃኒት።--በማቴዎስ 11፡ 28 ላይ ‹‹ወደ እኔ ኑ… እረፍት እሰጣችኋለሁ›› የሚሉት የአዳኛችን ቃላት አካላዊውን፣ አእምሮአዊውንና መንፈሳዊውን በሽታዎች ለመፈወስ የታዘዙ ናቸው። ሰዎች በራሳቸው ስህተት ሥቃይን በራሳቸው ላይ ቢያመጡም እርሱ በሀዘኔታ ይመለከታቸዋል። ከእርሱ እርዳታ ያገኛሉ። በእርሱ ለሚታመኑት ታላላቅ ነገሮችን ያደርግላቸዋል። --MH 115 (1905). {1MCP 66.1}1MCPAmh 55.3

    ወንጌል ከሳይንስና ከሥነ-ጽሁፍ ጋር ሲነጻጸር።--ጨለማ በሆነው የሰዎች አእምሮ ውስጥ በግርማ የተሞላው የእግዚአብሔር ልጅ ወንጌል ሊያመጣ የሚችለውን ብርሃን ሳይንስና ሥነ-ጽሁፍ ሊያመጡ አይችሉም። ነፍስን የማብራትን ታላቅ ሥራ መሥራት የሚችል የእግዚአብሔር ልጅ ብቻ ነው። ስለዚህ ጳውሎስ ‹‹በወንጌል አላፍርምና የእግዚአብሔር ኃይል ነውና ለመድኃኒት ለሚያምኑት ለአይሁድ አስቀድሞ ለአረማውያንም ደግሞ›› (ሮሜ 1፡ 16) ብሎ መናገሩ አያስደንቅም። በሚያምኑ ሰዎች ውስጥ የክርስቶስ ወንጌል ማንነት ይሆንና በሁሉም ሰዎች ፊት የሚታወቁና የሚነበቡ ደብዳቤዎች እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል። በዚህ መንገድ እግዚአብሔርን የመምሰል እርሾ ወደ ብዙ ሰዎች ያልፋል። በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ብቃት የሚታየው በጎነት ብቻ ስለሆነ የሰማይ ኃይላት በባሕርይ ውስጥ ታላቅነትን የሚያመጡ እውነተኛ ነገሮችን ለይተው ማየት ይችላሉ። --RH, Dec 15, 1891. (FE 199, 200.) {1MCP 66.2}1MCPAmh 56.1

    ህብረተሰብን እያጠፉ ያሉ ክፋቶችን ወንጌል ብቻ ሊፈውስ ይችላል።--ለሰዎች ኃጢአትና ሀዘን ብቸኛው ፈውስ ክርስቶስ ነው። ማህበረሰብን እያጠፉ ያሉ ክፋቶችን መፈወስ የሚችል የእርሱ የጸጋ ወንጌል ብቻ ነው። ሀብታሞች በድሆች ላይ የሚፈጽሙት ኢ-ፍትሃዊነት፣ ድሆች በሀብታሞች ላይ ያላቸው ጥላቻ፣ መነሻቸው በተመሳሳይ ሁኔታ ራስ ወዳድነት ስለሆነ ይህ ሊጠፋ የሚችለው ለክርስቶስ በመገዛት ብቻ ነው። ኃጢአተኛ ለሆነው ራስ ወዳድ ልብ አዲስ የሆነ የፍቅር ልብ የሚሰጠው እርሱ ብቻ ነው። እርሱ ከሰማይ በተላከ መንፈስ ወንጌልን በመስበክ ለሰዎች ጥቅም እንደሰራ ሁሉ የክርስቶስ ባርያዎችም እንዲሁ ይስሩ። ያኔ በሰብአዊ ኃይል በፍጹም ሊፈጸሙ የማይችሉ፣ የሰውን ዘር የሚባርኩና ከፍ የሚያደርጉ ውጤቶች ይታያሉ።--COL 254 (1900). {1MCP 66.3}1MCPAmh 56.2

    ፍጽምና ሊደረስበት የሚችለው በተጣጣመ እድገት ብቻ ነው።--የአእምሮ መሻሻል ለራሳችን፣ ለህብረተሰባችንና ለእግዚአብሔር ባለዕዳ የሆንንበት ተግባር ነው። ነገር ግን ግብረገብንና መንፈሳዊ ነገሮችን ችላ በማለት አእምሮን የምናሳድግበትን ዘዴ በፍጹም መቀየስ የለብንም። ወደ ማንኛውም ከፍተኛ ፍጽምና ሊደረስበት የሚቻለው የአእምሮና የግብረገብ ኃይሎች በተጣጣመ ሁኔታ ሲያድጉ ብቻ ነው። --CT 541 (1913). {1MCP 67.1}1MCPAmh 56.3

    መለኮታዊው እርሾ አእምሮን ይለውጣል።--በምሳሌው ሴትዮዋ እርሾን በምግብ ውስጥ ጨመረች። የሚያስፈልገውን ነገር መስጠት አስፈላጊ ነበር።…ስለዚህ መለኮታዊው እርሾም ሥራውን ይሰራል።…አእምሮ ይለወጣል፤ የተለያዩ የአካል ክፍሎች ለሥራ ይዘጋጃሉ። ሰው አዲስ የአካል ክፍሎች አይሰጡትም፣ ነገር ግን ያሉት የአካል ክፍሎች ይቀደሳሉ። ከዚህ በፊት ሞቶ የነበረው ህሊና ይነሳል። ነገር ግን ሰው በራሱ ይህን ለውጥ ማምጣት አይችልም። ይህን ማድረግ የሚችለው መንፈስ ቅዱስ ብቻ ነው። … {1MCP 67.2}1MCPAmh 56.4

    አእምሮዎቻችን በእግዚአብሔር መንፈስ ቁጥጥር ሥር በሚሆኑበት ጊዜ በእርሾው ምሳሌ የተሰጠውን ትምህርት እናስተውላለን። እውነትን ለመቀበል ልባቸውን የሚከፍቱ ሰዎች የእግዚአብሔር ቃል የሰዎችን ባሕርይ ለመቀየር ትልቁ መሳሪያ እንደሆነ ይገነዘባሉ። --RH, July 25, 1899. {1MCP 67.3}1MCPAmh 57.1

    የወንጌል እውነት የማይናወጥ ዓላማን ይሰጣል።--እያንዳንዳችን የእግዚአብሔር ቃል ለሚያስተምረን ነገሮች ጥልቅ መረዳት ያስፈልገናል። አእምሮዎቻችን ከውስጥ ወይም ከውጭ የሚመጣውን እያንዳንዱን ፈተና ለመቋቋምና ለማሸነፍ ዝግጁ መሆን አለባቸው። አሁን እንደምናምነው የምናምነው ለምን እንደሆነ፣ ለምን በጌታ ወገን እንደምንቆም ማወቅ አለብን። እውነት በልባችን ውስጥ የማስጠንቀቂያ ድምጽ ለማሰማትና እያንዳንዱን ጠላት ለመዋጋት እርምጃ እንድንወስድ ጥሪ ለማቅረብ በመዘጋጀት ነቅቶ መጠበቅ አለበት። የጨለማ ኃይሎች የከባድ መሳሪያ ተኩስ ይከፍቱብናል፣ ቸልተኞችና ግድ የለሾች፣ ልባቸውን በምድራዊ ሀብታቸው ላይ ያደረጉ እና እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር እንዴት እንደሚሰራ ለማወቅ ግድ የሌላቸው በቀላሉ በጠላት ይጠቃሉ። እውነትን በኢየሱስ እንዳለ ከማወቅ ውጭ ማንኛውም ኃይል የማንናወጥ ሊያደርገን አይችልም፤ ነገር ግን በዚህ አማካይነት አንድ ሰው አንድ ሺህ ሰዎችን፣ ሁለት ሰዎች ደግሞ አሥር ሺህ ሰዎችን ሊያባርሩ ይችላሉ። --RH, Apr 29, 1884. (HC 332.) {1MCP 67.4}1MCPAmh 57.2

    ራሳችንን ለክርስቶስ አሳልፈን መስጠት ሰላምን ያመጣል።--የወደፊት ሁኔታችን ሙሉ በሙሉ የሚያርፈው የሰላም ልዑልን ለመቀበል ልባችንን ለመክፈት በምናደርገው የግል እርምጃችን ላይ ነው። አእምሮዎቻችን ፀጥታና እረፍት ማግኘት የሚችሉት የኃይል ብቃት ባለው በክርስቶስ በመሆናችንና ራሳችንን ለእርሱ አሳልፈን በመስጠታችን ነው። እርሱ ለነፍስህ የሚሰጠውን ያንን ሰላም፣ ያንን መጽናናት፣ ያንን ተስፋ የራስህ ስታደርግ፣ እንደ ግለሰብ ለአንተ ለቀረበልህ ታላቅና አስደናቂ ለሆነው ተስፋ እውቅና ስትሰጥ፣ ልብህ አዳኛችን በሆነው በእግዚአብሔር ሀሴት ያደርጋል። ያኔ ለተሰጠህ ታላቅ ፍቅርና ፀጋ እጅግ አመስጋኝ ስለምትሆን እግዚአብሔርን ታወድሳለህ።--{1MCP 68.1}1MCPAmh 57.3

    ረዳትህን ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከት። እንኳን ደህና መጣህልኝ በማለት የእርሱን በጸጋ የተሞላ መገኘት ጋብዝ። አእምሮህ በየዕለቱ ስለሚታደስ ሰላምና ዕረፍትን መቀበል፣ ከጭንቀት በላይ ከፍ ማለት እና ለበረከቶችህ እግዚአብሔርን ማመስገን ለአንተ መልካም ዕድል ነው። ክርስቶስ ከነፍስህ እንዲርቅ የሚያደርጉ የሚያስጠሉ ነገሮችን አጥር አትጠር። ድምጽህን ቀይር፤ አትዘን፤ ክርስቶስ ከዚህ በፊት ላሳየህና አሁንም እያሳየህ ላለው ታላቅ ፍቅር አመስጋኝነትህን አሳይ።--Lt 294, 1906. {1MCP 68.2}1MCPAmh 57.4

    በክርስቶስ መኖር ማበረታቻን ይሰጣል።--አእምሮዎቻችን በክርስቶስና በሰማያዊው ዓለም እንዲኖሩ ብንፈቅድ ኖሮ የጌታን ጦርነት ለመዋጋት ኃይለኛ የሆነ ማበረታቻና ድጋፍ እናገኝ ነበር። በቅርቡ ቤታችን ሊሆን ባለው በተሻለው ምድር ክብር ላይ ስናሰላስል ኩራትና የዓለም ፍቅር ኃይላቸውን ያጣሉ። የክርስቶስን ውበት ስንመለከት ምድር የምታቀርባቸው የሚስቡ ነገሮች ሁሉ ዋጋ ያጣሉ። --RH, Nov 15, 1887. {1MCP 68.3}1MCPAmh 58.1

    እውቀት አእምሮንና ነፍስን ያጠነክራል።--የሚያስፈልገን አእምሮንና ነፍስን የሚያጠነክር፣ የተሻልን ወንዶችና ሴቶች እንድንሆን የሚያደርገን እውቀት ነው። ዝም ብሎ ከመጻሕፍት ከመማር ይልቅ የልብ ትምህርት እጅግ የላቀ ጥቅም አለው። ስለምንኖርበት ዓለም እውቀት ማግኘት ጥሩና አስፈላጊ ነው፤ ነገር ግን ዘላለማዊነትን ከቁጥር ውስጥ ሳናስገባ ሲቀር በፍጹም መመለስ የማንችልበትን ስህተት እንፈጽማለን። --MH 450 (1905). {1MCP 68.4}1MCPAmh 58.2

    አእምሮና መንፈሳዊ ጦርነት።--በግብረገብ ንጽህና መሻሻል ማሳየታችን የሚደገፈው በትክክል በማሰባችንና በትክክል በመስራታችን ነው። ‹‹ሰውን የሚያረክሰው ወደ አፍ የሚገባ ሳይሆን ከአፍ የሚወጣው ነገር ነው።›› ‹‹ክፉ አሳብ፣ መግደል፣ ምንዝር፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ በውሸት መመስከር እና ስድብ የሚወጣው ከልብ ነው። ሰውን የሚያረክሱት እነዚህ ነገሮች ናቸው›› (ማቴ. 15፡ 11፣ 19፣ 20)። --{1MCP 69.1}1MCPAmh 58.3

    ክፉ አሳቦች ነፍስን ያጠፋሉ።--የእግዚአብሔር የመለወጥ ኃይል አሳብን በመሞረድና በማንጻት ልብን ይለውጣል። አሳብ ክርስቶስን ማዕከል እንዲያደርግ የማያወላዳ ጥረት ካልተደረገ በስተቀር ጸጋ ራሱን በሕይወት ውስጥ ማሳየት አይችልም። አእምሮ በመንፈሳዊ ጦርነት ለይ መጠመድ አለበት። እያንዳንዱ አሳብ ለክርስቶስ ለመታዘዝ ምርኮኛ መሆን አለበት። ልምዶች ሁሉ በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር መሆን አለባቸው። --Lt 123 1904. {1MCP 69.2}1MCPAmh 58.4

    አእምሮን አስቀድሞ በመልካም ነገር እንዲጠመድ ማድረግ ከክፉ ይጠብቃል።--ከክፉ ለመጠበቅ አእምሮን በመልካም ነገር እንዲያዝ ማድረግ ቁጥር ስፍር ከሌላቸው የሕግና የዲስፕሊን መከላከያዎች የበለጠ ዋጋ አለው። --Ed 213 (1903). {1MCP 69.3}1MCPAmh 58.5

    የተዛባ ግምት (አሳብ) ጨለማን ያመጣል።--የአእምሮ ዓይን እግዚአብሔርን የመምሰልን ምስጢር መልካምነት፣ መንፈሳዊ ሀብቶች ከዓለማዊ ሀብቶች ይልቅ ያላቸውን ብልጫ ቢያይ ኖሮ መላው አካል በብርሃን የተሞላ ይሆን ነበር። ጥቅምን ማግኘት እግዚአብሔርን መምሰል እስኪመስል ድረስ አሳብ በምድራዊ ጉራና ድምቀት ውበት ከተዛባ መላው አካል በጨለማ ይሞላል። የአእምሮ ኃይሎች በምድራዊ ሀብቶች ላይ በሚያተኩሩበት ጊዜ እጅግ የወረዱና ያነሱ ይሆናሉ።--RH, Sept 18, 1888.70 {1MCP 69.4}1MCPAmh 59.1

    ራስን ከፍ ወደ ማድረግ ሳይሆን ወደ ፈጣሪ የተመለሰ አእምሮ።--ይህ መርህ [ለእግዚአብሔር ክብር መሥራት] የሚሰጠው ጥቅም የሚጠይቀውን ያህል ትኩረት ቢሰጠው ኖሮ ዛሬ ባሉ በአንዳንድ የትምህርት ዘዴዎች ላይ መሰረታዊ የሆነ ለውጥ ይኖር ነበር። የመኮረጅን መንፈስ በማቀጣጠል ለኩራትና ለራስ ምኞት ከመጓጓት ይልቅ፣ መምህራን ለመልካምነት፣ ለእውነትና ለውበት ያለውን ፍቅር ለመቀስቀስ- ከሁሉ በልጦ የመገኘት ፍላጎትን ለማነሳሳት- ጥረት ያደርጉ ነበር። ተራ ወደሆኑ ምድራዊ መስፈርቶች ከመመራት ወይም አእምሮ ቀጭጮና አንሶ እንዲገኝ በሚያደርግ ራስን ከፍ ከፍ የማድረግ ፍላጎት ከመንቀሳቀስ ይልቅ አእምሮ ወደ ፈጣሪ፣ እርሱን ወደ ማወቅና ወደ መምሰል ይመራል።--PP 595, 596 (1890). {1MCP 70.1}1MCPAmh 59.2

    ሕያው ውኃና የሚያፈሱ (የተሸነቆሩ) ገንዳዎች ንጽጽር።--ኢየሱስ የነፍስን ጉድለቶች ያውቅ ነበር። ጉራ፣ ሀብትና ክብር ልብን ማርካት አይችሉም። ‹‹ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣ።›› ሀብታሞች፣ ድሆች፣ ከፍተኞች፣ ዝቅተኞች፣ ሁሉም በእኩል ተቀባይነት ያገኛሉ። እርሱ ጫና የበዛበትን አእምሮ ለማሳረፍ፣ ያዘኑትን ለማጽናናት እና ተስፋ ለቆረጡት ተስፋ ለመስጠት ቃል ገብቷል። {1MCP 70.2}1MCPAmh 59.3

    ኢየሱስን ይሰሙ ከነበሩት አብዛኞቹ ሳይፈጸሙላቸው ከቀሩት ተስፋዎች የተነሣ ተስፋ የቆረጡ ነበሩ፣ ብዙዎቹ እረፍት የሌለውን ናፍቆታቸውን በዓለም ነገሮችና በሰዎች ሙገሳ ለማርካት የሚሹ ነበሩ፤ ነገር ግን የፈለጉትን ሁሉ ካገኙ በኋላ የተረዱት ነገር ቢኖር ልፋታቸው ሁሉ ጥማታቸውን ለማርካት ወደማይችሉ የተሸነቆሩ የውኃ ገንዳዎች ጋ ለመድረስ ብቻ እንደሆነ ነበር። በቦታው በነበረው የደስታ ብልጭልጭ ውስጥ እርካታ አጥተውና አዝነው ቁመው ነበር። {1MCP 70.3}1MCPAmh 59.4

    ‹‹ማንም የተጠማ ቢኖር›› የሚለው አሳዛኝ ጩኸት በሀዘን ቆዝመው ከሚያሰላስሉበት ሁኔታ ቀሰቀሳቸውና ቀጥለው የነበሩ ቃላትን ሲሰሙ አእምሮዎቻቸው በአዲስ ተስፋ ተቀጣጠሉ። የድነትን በዋጋ የማይተመን ሥጦታ በውስጡ እስኪመለከቱ ድረስ መንፈስ ቅዱስ በፊታቸው ምልክት አቀረበላቸው። --DA 454 (1898). {1MCP 70.4}1MCPAmh 59.5

    የሰብአዊና መለኮታዊ ጥረት አንድነት አስፈላጊ ነው።--በእያንዳንዱ አጣዳፊ ሁኔታ ውስጥ-ፍቅር በሌላቸው ዘመዶች መካከል፣ በዓለም ጥላቻ መካከል እና የራሳቸውን ፍጹማን አለመሆንና ስህተቶች ከመገንዘብ የተነሣ እየተፍጨረጨሩና እየታገሉ ላሉ ነፍሳት መንፈስ ብርታትን ይሰጣል። የሰብአዊና መለኮታዊ ጥረት አንድነት፣ የብርታት ሁሉ ምንጭ ከሆነው ከእግዚአብሔር ጋር የመጀመሪያ፣ የመጨረሻና ለሁል ጊዜም የቀረበ ግንኙነት መፍጠር ሙሉ ለሙሉ አስፈላጊ ነው።--RH, May 19, 1904. (HC 151.) {1MCP 70.5}1MCPAmh 60.1

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents