Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

የአድቬንቲስት ቤት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ ሃምሳ አምስት—የግብረ-ገብነት ደረጃዎች

    ሰይጣን የጋብቻን ተቋም ለማዛባት ይሻል፦ የጋብቻን ተቋም ለማበላሸት፣ ቅድስናውን ለመቀነስና ግዴታዎቹን ለማዳከም በውኃ ጥፋት ዘመን የሰይጣን የተጠና ጥረት ነበር። የእግዚአብሔርን መልክ በሰው ዘንድ በማበላሸት የመከራና የዝሙት በርን መክፈት የሚችልበት ከዚህ የበለጠ መንገድ እንደሌለው ያውቃል። 1Patriarchs and Prophets, p. 338.AHAmh 234.1

    በሰው ልብ ውስጥ በምን ዓይነት መሣሪያ መሥራት እንዳለበት ሰይጣን ጠንቅቆ ያውቃል። በዳያቢሎሳዊ ጥልቅ ትኩረት ለብዙ ሺህ ዓመታት አጥንቷል - በእያንዳንዱ ባህርይ ውስጥ በቀላሉ ሊጠቁ የሚችሉትን ቦታዎች ያውቃቸዋል። በበኣል ጴኦር እጅግ ውጤታማ በነበሩት ማሳሳቻዎቹ ሲወርድ ሲዋረድ በመጣው ትውልድ፣ በኃያላን ሰዎችና በእስራኤል ልዑላን ላይ ውድቀትን አምጥቷል። በስሜት እርካታ ቋጥኝ ላይ ተንኮታኩተው ሆጭ እንዳሉ፣ የተተዉ ለዘመናት የተበታተኑ የባህርይ ስብርባሪዎች ሞልተዋል። 2Id., p. 457.AHAmh 234.2

    አሳዛኝ ክስተት በእስራኤል፦ ፍርድ በእስራኤል ላይ እንዲመጣ ያደረገው ጥፋት መንስኤው ወሲባዊ ልቅነታቸው ነበር። የሴቶች ሐፍረተ-ቢስ የሆነው ነፍስን የማጥመድ ጥረታቸው፣ በበኣል ጴኦር ተወስኖ አልቀረም ነበር። ኃጢአት የሠሩት ምን ዓይነት ቅጣት እንደገጠማቸው ግልጽ ሆኖ እያለ ያው ጥፋት ለብዙ ጊዜ በተደጋጋሚ ይፈጸም ነበር፤ የእስራኤል መገልበጥ ክንውን ያገኝ ዘንድ ሰይጣን በፍጹም ትጋት እራሱ ይሠራ ነበር። 3Review and Herald, May 17, 1887.AHAmh 234.3

    ለዕብራዊያኑ የአሕዛብ የጦር ዕቃና የበለዓም እርግማን ማከናወን ያልቻለውን የወሲብ ገደብ-የለሽነታቸው ፈጸመው። ከእግዚአብሔር የተነጣጠሉ ሆኑ፤ መደበቂያና መጠባበቂያቸው ከእነርሱ ተወሰደ፤ እግዚአብሔር ጠላታቸው ሆነ። ብዙዎቹ ልዑላንና ሕዝቡ የወሲባዊ ልቅነት ጥፋተኞች ሆነው ኃጢአቱ ብሔራዊ ሆነ፤ እግዚአብሔር በሕዝቡ ሁሉ ላይ ተቆጥቶ ነበርና። 4Review and Herald, May 17, 1887.AHAmh 234.4

    ታሪኩ ይደገማል፦ የዚህ ዓለም ታሪክ መደምደሚያው ሲቃረብ ጥንታዊ እስራኤላዊያን ወደ ተስፋይቱ ምድር ሊገቡ በተቃረቡበት ጊዜ በተፈተኑባቸው ተመሳሳይ ፈተናዎች ሰይጣን ሙሉ ኃይሉን ተጠቅሞ ለማሳሳት ተግቶ ይሠራል። ወደ ሰማያዊ ከነዓን ድንበር ለተጠጉት የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት እንከተላለን ለሚሉት ሰዎች ሰይጣን ወጥመድ ያዘጋጃል። ኃይሉን ሁሉ ተጠቅሞ በእግዚአብሔር ሕዝብ ደካማ ጎኖች ላይ በመሥራት ነፍሳትን ያጠምዳል። የረከሰውን ፍላጎታቸውን የሚያሳድዱትን፤ ለከፍተኛው ተፈጥሮአዊ ኃይላቸው እራሳቸውን ያላስገዙትን፤ በተዋረደው የሥጋዊ ፍላጎታቸው ጅረት ሐሳባቸው እንዲፈስ የፈቀዱትን ሰይጣን በፈተናው አሰናክሎ ሊያጠፋቸው ቁርጠኛ ነው። በወሲባዊ ልቅነት ነፍሳቸውን ሊበክለው ተዘጋጅቷል። ዝቅተኛና ብዙም አስፈላጊ ባልሆኑ ኢላማዎች ላይ አያነጣጥርም። የእርሱ ወኪል እንደሆኑ በሚተማመንባቸው ሰዎች አማካይነት ወጥመዱን ሥራ ላይ በማዋል በእግዚአብሔር የሕግ መነጽር ሲታዩ በሚወገዙት የነፃነት መሥመሮች እንዲታለሉ ያደርጋል። ሰይጣን ሥራቸውን ሊያመክን ወረራ የጀመረባቸው የእግዚአብሔርን ሕግ መጠይቅ የሚያስተምሩ የአምላክን ሕግ እውነተኛነት በማስረዳት አፋቸው የተሞላ በኃላፊነት የተቀመጡ ሰዎች አሉ። በእንደዚህ ዓይነቶቹ ሰዎች ላይ ኃይለኛ ጉልበቱን በማፍሰስ ወኪሎቹን በሥራ በመጥመድ ደካማ የባህርይ ጎናቸውን ተጠቅሞ አንዱን የተላለፈ ሁሉንም ተላለፈ በሚለው መሠረት ሰውን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥሩ ሥር ያደርጋል። አዕምሮ፣ ነፍስ፣ አካል እንዲሁም ንቃተ-ሕሊና የጥፋቱ አካል ይሆናሉ። ይህ [የተሸነፈው] ሰው የጽድቅ መልእክተኛ የታላቅ ብርሃን ባለቤት ወይም እግዚአብሔር ለእውነት ያቆመው የእርሱ የተለየ ሠራተኛ ከሆነ የሰይጣን ድል እንዴት ታላቅ ይሆን! እንዴትስ ይፈነጥዝ ይሆን! እግዚአብሔር እንዴት ይዋረድ ይሆን! 5Review and Herald, May 17, 1887.AHAmh 234.5

    የግብረ-ገብነት እጦት መስፋፋት በዛሬው ዘመን፦ ዓለም ያለበት አስከፊው ሁኔታ በምስል በፊቴ ቀርቦልኛል። የግብረ-ገብነት ዕጦት በሁሉም ቦታ ተስፋፍቷል፤ ወሲባዊ ልቅነት የዘመኑ የተለየ ኃጢአት ሆኗል። ዝሙት ቅጥ ያጣ ጭንቅላቱን በኩራት ከፍ አድርጎ የሚሄድበት እንደ አሁኑ ያለ ጊዜ አልነበረም። ሰዎች እየደነዙ ናቸው። እውነተኛ መልካምነትንና ስነ-ምግባርን የሚወድዱ እነርሱ በድፍረቱ በጥንካሬውና በመስፋፋቱ ምክንያት ተስፋ ወደ መቁረጥ ተቃርበዋል። እያጥለቀለቀ ያለው ርኩሰት በማያምኑና በፌዘኞች ብቻ የተወሰነ አይደለም። ያስ ቢሆን ኖሮ ይሻል ነበር፤ ግን አይደለም። የክርስቶስን ኃይማኖት የሚሰብኩ ብዙ ወንዶችና ሴቶች ጥፋተኞች ናቸው። መገለጹን እንጠባበቃለን የሚሉት እንኳን አንዳንዶቹ ሰይጣን ለዚያ ቀን ከተዘጋጀበት የተሻለ ዝግጅት አላደረጉም። እራሳቸውን ከብክነት እያነፁ አይደሉም፤ ለፍላጎታቸው ተገዢ ሆነው አስተሳሰባቸው ቆሻሻ፣ ዓይነ-ህሌናቸው ብልሹ መሆኑን እንደተለመደ ተፈጥሮአዊ ክስተት ይመለከቱታል። የኒያጋራን ወንዝ ፏፏቴ ሽቅብ እንዲፈስ ማድረግ እንደማይቻል ሁሉ ሕሊናቸው በንጹህና በቅዱስ ነገሮች ውስጥ እንዲኖር ማድረግ የማይሞከር ነው.... ፍላጎቱን ሊገድብና መርሆው ሊቆጣጠረው ይችል ዘንድ እያንዳንዱ ክርስቲያን መማር ያስፈልገዋል። ይህንን ካላደረገ በስተቀር የክርስቲያን ስም የተገባው አይደለም። 6Testimonies for the Church, Vol. 2, pp. 346, 347.AHAmh 235.1

    የፍቅር ሕመምተኛነትና ስሜታዊነት ተስፋፍቷል። ያገቡ ወንዶች ካገቡ ወይም ካላገቡ ሴቶች ትኩረት ይቸራቸዋል። ሴቶች መስሜት ተውጠው የማገናዘብ፣ የመንፈሳዊ ዕውቀትና የማመዛዘን ችሎታቸውን ያጣሉ። የእግዚአብሔር ቃል የሚያወግዛቸውን ነገሮች የጌታ ቅዱስ መንፈስ ምስክሮች በፍጹም የሚከለክሏቸውን እነዚያውኑ ርኩሰቶች ሲፈጽሙ ይገኛሉ። ማስጠንቀቂያና ተግሳጽ በፊታቸው ተቀምጠውላቸዋል። ሆኖም ከእነሱ በፊት ሌሎች በተራመዱበት መንገድ ይሄዳሉ። በሚያቅበጠብጥ ግጥሚያ (game) ውስጥ ሆነው የሚጫወቱ ይመስላሉ። የአምላክን ዓላማ አደጋ ላይ ለመጣል የእግዚአብሔርን ልጅ እንደገና ለመስቀልና በአደባባይ ለማዋረድ ሲል እራሳቸውን እንዲያጠፉ ሰይጣን ይመራቸዋል። 7Manuscript 19a, 1890.AHAmh 236.1

    የድንቁርና፣ የተድላ ፍቅርና የጥፋት ልማዶች ነፍስን፣ አካልንና መንፈስን በማበላሸት ዓለምን በግብረ-ገብነት ቁምጥና ሞልቶታል። ገዳዩ የግብረ-ገብነት ወግ እልፍ አእላፋትን እያጠፋ ነው። ወጣቱን ለመታደግ ምን ቢደረግ ይሻላል? እኛ ማድረግ የምንችለው በጣም ጥቂቱን ነው፤ ሕያውና የበላይ የሆነው እግዚአብሔር ግን ብዙ ማድረግ ይችላል። 8Manuscript 8, 1894.AHAmh 236.2

    የእግዚአብሔር ሕዝቦች ከዓለም ተለይተው መቆም ይገባቸዋል፦ ይህ የተበላሸ ዓለም የሚሰጠው ነፃነት ለክርስቶስ ተከታዮች መመዘኛ ሊሆን አይገባውም። እነዚህ ጊዜ-አመጣሽ ትርኢቶች ለዘለዓለም ገጣሚ በሚሆኑ ክርስቲያኖች መካከል መከሰት የለባቸውም። ሐፍረተ-ቢስነት ብክለተ-ዝሙት ወንጀልና ነፍሰ-ገዳይነት እውነትን በማያውቁ የእግዚአብሔር ቃል በመመሪያነት ሊቆጣጠራቸው እምቢ ባሉ ሰዎች መካከል ተንሰራፍቷል። ይህን ሥር የሰደደ ርኩሰት ገሃድ በማውጣት ክርስቶስን እንከተላለን የሚለው የሕብረተሰብ ክፍል ከእግዚአብሔርና ከመላእክት ጋር በቅርበት በመተባበር ለነዚህ ለወደቁ ነፍሳት የተሻለና የከበረ መንገድ ሊያሳያቸው እንዴት አስፈላጊ ነው! የጌታ ልጆች በመልካም ባህርያቸውና በንጽሕና በመቆማቸው ፍላጎት ከተቆጣጠራቸው ሰዎች ተነጥለው በሚስተዋል ልዩነት ሊቆሙ እንዴት አስፈላጊ ነው! 9Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 459.AHAmh 236.3

    የስጋትና የአደጋዎች መጨመር፦ በዚህ የተበላሸ ዘመን በኃጢአት ርኩስነት የታወሩ ሕገ-ወጥ የሆነ ሕይወትን የመረጡ ብዙ ሰዎች ይገኛሉ፤ ምክንያቱ ደግሞ የሚከተሉት መንገድ የልባቸውን ተፈጥሮአዊና የተጣመመ ዝንባሌ ስለሚገጥም ነው። የእግዚአብሔርን የሕግ መስታወት እንደመመልከት፤ ልባቸውንና ባህርያቸውን ከፍ አድርገው ወደ እግዚአብሔር ደረጃ እንደማምጣት፤ የአጥፊውን የባህርይ ደረጃ በልባቸው እንዲተክሉ ለሰይጣን ወኪሎች ይፈቅዱላቸዋል። ምግባረ-ብልሹ የሆኑ ወንዶች ኃጢአታቸውንና ብልሹነታቸውን በመተው በልባቸውና በሕይወታቸው ንጹህ ከመሆን ይልቅ ለጥፋታቸው እንዲስማማ አድርገው ቃሉን አዛብተው በመተርጎም በአመጽ መቀጠል ይቀልላቸዋል። እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ብዙዎች ከሚያስቡት በላይ በቁጥር የበዙ ናቸው፤ ወደ ቀኑ መጨረሻ በተቃረብን መጠን የበለጠ እየበዙ ይሄዳሉ። 10Id., Vol. 5, p. 141.AHAmh 236.4

    የሚያነሆልለው የሰይጣን ኃይል ነፍስን ሲቆጣጠረው እግዚአብሔርን ይረሳና በተበከለ ምግባር የተሞላ፣ በከንቱ ውዳሴ የተሸነገለ ሰው ይፈጠራል፤ ምስጢራዊ ሕገወጥነት በነዚህ በተታለሉ ነፍሳት እንደ ባህርይ ሆኖ ይተገበራል። ይህ የጥንቆላ ዝርያ ነው…. በአፈንጋጭነትና በሕገ-ወጥነት ምንጊዜም የሚያደነዝዝ ኃይል አለ። አዕምሮአቸው በፍጹም ሞኝነት ተሸፍኖ በጥበብ ማገናዘብ ይሳነዋል፤ የተሳሳተ ግንዛቤው ከንጽህና ያርቀዋል፤ መንፈሳዊ የማየት ችሎታው የደበዘዘ ይሆናል። ሳይበከል የቆየው የሰዎች ሥነ-ምግባር እውነት የሚመስል የማሳሳት ኃይል በያዙ የብርሃን መልእክተኛነታቸውን በገሃድ ባወጁ የሰይጣን ወኪሎች ግራ ይጋባል። ይህ የማሳሳት ጥበብ የዲያብሎስ ሥራ አስፈፃሚዎች ኃይል ነው። በድፍረት ቢወጡና እንቅስቃሴአቸውን በገሃድ ቢያራምዱ፣ ያለምንም ማመንታት ወዲያውኑ ተቃውሞ ይገጥማቸው ነበር፤ ሆኖም በመጀመሪያ አንጀት የመብላት ስሜትን ለመፍጠር፣ በመሥራት ቅዱስና ራሳቸውን በመስዋዕትነት የሚያቀርቡ የእግዚአብሔር ሰዎች እንደሆኑ በማስመሰል አመኔታን ያተርፋሉ። ከዚያም እንደ ልዩ መልእክተኞች የጮሌነት ሥራቸውን በመቀጠል፣ የእግዚአብሔርን ሕግ ለማፍረስ በማንገራገር ነፍሳትን ከቀጥተኛው መንገድ ይጎትቷቸዋል። 11Id., pp. 142, 143.AHAmh 237.1

    ወንዶችና ሴቶች ደረጃቸውን በመጠበቅ ከአሳፋሪነት በላይ መኖር ይገባቸዋል፦ የወንድ ወይም የሴት አዕምሮ ከንጽህናና ከቅድስና ከፍታው ወደ ሥነ-ምግባር ዝቅጠት፣ ብልሹነትና ወንጀል በአንድ ጊዜ አይወርድም። ሰውን ወደ ቅድስና ለማምጣት ወይም በእግዚአብሔር ምሣሌ የተሠሩትን ዝቅ በማድረግ ወደ ጭካኔና ወደ ሰይጣናዊነት ለመቀየር ጊዜ ይወስዳል። በማየት እንለወጣለን፤ በፈጣሪው አምሣል የተሠራ ቢሆንም ሰው በአንድ ወቅት ያንገሸግሸው የነበረው ኃጢአት አስደሳች ይሆንለት ዘንድ አዕምሮውን ያስተምራል። መጠንቀቅና መፀለይ ሲያቆም ምሽጉ የሆነውን ልቡን መጠበቅ ይተውና በኃጢአትና በወንጀል ይጠመዳል። የግብረ-ገብነትና የሕሊና ኃይላትም በጸያፍ ፍላጎት ዕዝ ሥር እንዲሆኑ መማር እስካላቆመ ድረስ አእምሮው ረክሷልና ከብልሹነቱ ማላቀቅ ፈጽሞ የማይቻል ነው። ከሥጋ ሐሳብ ጋር ያለው ጦርነት መቀጠል አለበት። አዕምሮውን ወደ ላይ በመሳብ በንጹህና በተቀደሱ ነገሮች ላይ የመመሰጥ ልምምድን እንዲያደርግ በሚያነጥረው የእግዚአብሔር ፀጋ ሊታገዝ ይ ገባዋል። 12Id., Vol. 2, pp. 478, 479.AHAmh 237.2

    በእያንዳንዱ እርምጃ የእግዚአብሔርን ምክር የመሻት ፍላጎት በወጣትም ሆነ በሽማግሌ ውስጥ እስከሌለ ድረስ ለሰው ደህንነት የለም። ከእግዚአብሔር ጋር የተቀራረበ ሕብረት የሚያደርጉ እነርሱ ብቻ ጌታ በሰዎች ላይ ያለውን ግምት በማስተዋል ንጹሁን፣ መልካሙን፣ ትሁቱንና የዋሁን ማወደስ ይችላሉ። የዮሴፍ ልብ ምሽግ ውስጥ እንደነበረ ሁሉ የሰው ልብ ቅጥር ሊሠራለት ይገባል። ከዚያም ፈተና ተወግዶ ቅንነት በውሳኔ ይለሰናል:- “ይህንን ታላቅ ስንፍና ላደርግ እግዚአብሔርን ልበድል እንዴት ይቻለኛል?” ተወዳዳሪ የሌለው ፈተና እንኳ ኃጢአት ለመሥራት እንደ ምክንያት ሊቀርብ አይችልም። ሸክማችሁ ምንም ያህል ከባድ ቢሆን ኃጢአት የራሳችሁ ሥራ ነው። የችግሩ ምክንያት ደግሞ ያልተለወጠውና ያልታደሰው ልብ ነው። 13Manuscript 19a, 1890.AHAmh 237.3

    ሁሉንም ኃጢአት፣ እያንዳንዱን መተላለፍና ጠማማነት ከመካከላችን ማስወገድ የለብንምን? ትንሹዋ የጥፋት መበረታቻ እንኳ ጥበቃ ሊደረግለት ወደማይችልልምምድ አሳልፋ እንዳትሰጣቸው እውነትን የሚናገሩ ሰዎች እራሳቸውን በጥበብ መቆጣጠር የለባቸውምን? ሁልጊዜ ጥብቅ የታቀበና ምሥጉን ጠባይ እንዲኖራቸው ቢተጉ ብዙ የፈተና በሮችን ጥርቅም አድርገው ሊዘጉ ይችላሉ። 14Testimonies for the Church, Vol. 5, pp. 601, 602.AHAmh 238.1

    ሴቶች ከፍ ያለውን የጠባይ ደረጃ ሊጠብቁ ይገባል፦ ያገቡም ሆነ ያላገቡ የዚህ ዘመን ሴቶች፣ ብዙውን ጊዜ አስፈላጊውን ጭምትነት መጠበቅ እንደተሳናቸው ስጽፍ በሐዘን በተወጋ ልብ ነው። እንደ አሽኮርማሚዎች ይንቀሳቀሳሉ። ያገቡትንም ሆነ ያላገቡትን ወንዶች ፍላጎት ያነሳሳሉ። መርህ የመከተል ኃይላቸው ደካማ የሆነባቸው ሁሉ ወጥመዳቸው ውስጥ ይገባሉ። እነዚህ ነገሮች ያለ ቁጥጥር ከተለቀቁ የግብረገብነት፣ የስሜት ሕዋሳትን በመግደልና አዕምሮን በማሳወር የሚፈጸመው ጥፋት ኃጢአት መስሎ እንዳይታያቸው ያደርጋሉ። ሥርዓት አክባሪነትዋንና መረጋጋትዋን ብታስጠብቅ ኖሮ ወደ ጭንቅላትዋ ድርሽ የማይሉት ኃሳቦችና ፍላጎቶች አሁን ይቀሰቀሳሉ። ሕገ-ወጥ ዓላማ ወይም ዝንባሌ እራስዋ አይኖራት ይሆናል፤ ነገር ግን በር ቢከፈት ዘው ብለው ለመግባት የጎመዡትን ወንዶች ታበረታታለች። ጥንቁቅና ቁጥብ በመሆን፤ በገፍ የሚገኘውን ቅጥ ያጣ መብት ባለመጠቀም፤ ማረጋገጫ የሌለው ትኩረት ባለመቀበል፤ ነገር ግን ከፍ ያለ የግብረ-ገብነት ቃና በመጠበቅና ክቡር ወደ መሆን በማደግ ብዙ ርኩሰት ሊወገድ ይችላል። 15Manuscript 4a, 1885AHAmh 238.2

    በየጊዜው እግዚአብሔር ሊያሳየኝ ፈቃዱ በሆኑት ነገሮች ሁሉ ከባድ ጉድለት ያለባቸው እንደሆኑ ለእህቶች ለመናገር የረዥም ጊዜ እቅድ ነበረኝ፤ ከክፉ ነገር ሁሉ በመታቀብ ጥንቁቆች አይደሉም። እግዚአብሔርን ወደ መምሰል ማደግ ይችሉ ዘንድ ሴቶች ሁሉ ለባህርያቸው ትኩረት የሚሰጡ አይደሉም። የእግዚአብሔርን ፀጋ የተቀበሉ ሰዎች መሆን እንደሚገባቸው ንግግሮቻቸው እንኳ የተለዩና በጥሞና የተመረጡ አይደሉም። ከወንድሞች ጋር እጅግ የተላመዱ ናቸው። በዙሪያቸው ያንዣብባሉ፤ ወደ እነርሱም ዘንበል ይላሉ፤ አብሮነታቸውን የፈለጉት ይመስላሉ። በሚለግሷቸውም ትኩረት እጅግ ይደሰታሉ። AHAmh 238.3

    እግዚአብሔር የሰጠኝ ብርሃን እንደሚያሳየኝ እህቶቻችን ፈጽሞ የተለየ መንገድ መከተል አለባቸው፤ ቁጥብ መሆን ይገባቸዋል። ደፋርነታቸውን በመቀነስ “ሀፍረትንና ጥበብን [ራስ መግዛትን]” በውስጣቸው ማበረታታት ይገባቸዋል። እህቶችና ወንድሞች ሲገናኙ በብዛት የሚያወሩት ደስ የሚያሰኟቸውን (የሚያስቋቸውን) ፍሬ-ቢስ ወሬዎችን ነው። እግዚአብሔርን ስለመምሰል የሚናገሩ (እግዚያብሔርን እንፈራለን የሚሉት) ሴቶች በበዛ ቀልድ ቧልትና ሳቅ ይረካሉ። ይህ ተገቢ ያልሆነ ጠባይ የእግዚአብሔርን መንፈስ የሚያሳዝን ነው። እነዚህ ትዕይንቶች የሚገልጡት እውነተኛ የክርስቲያናዊ ንጥረት ጉድለትን ነው። ነፍስን በእግዚአብሔር አያበረቱም፤ ድቅድቅ ጨለማን ያመጣሉ እንጂ። በእነዚህ ጥፉዎች የሚጠመዱ ሁሉ ንጹሆቹንና የጠሩትን ሰማያዊ መላእክት አባርረው ዝቅ ወዳለ የሚያዋርድ ደረጃ ይዘቅጣሉ። 16Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 455.AHAmh 239.1

    ብዙውን ጊዜ የሚፈታተኑት ሴቶች ናቸው። በአንድ ሰበብ ወይም በሌላ የወንዶችን ቀልብ ይስባሉ። ያገቡትም ሆኑ ያላገቡት ወንዶች የእግዚአብሔርን ሕግ እስኪተላለፉ ድረስ ጠቃሚነታቸው እስኪመክንና ነፍሳቸው በአደጋ ላይ እሰኪወድቅ ድረስ ይመሯቸዋል…. ሴቶች ሕይወታቸውን ከፍ ከፍ አድርገው ከክርስቶስ ጋር ሠራተኞች ቢሆኑ በተጽዕኖአቸው የሚመጣው አደጋ በቀነሰ ነበር። ነገር ግን አሁን በሚታይባቸው ለቤት ኃላፊነት ቁብ አለመስጠትና እግዚአብሔር በእነርሱ ላይ ላለው መጠይቅ ግድ የለሽ ስሜታቸው ተጽዕኖአቸውን በተሳሳተ አቅጣጫ የጠነከረ ያደርገዋል። የመልካምነት ኃይላቸው የቆረቆዘ ነው። ሥራቸው መለኮትን የሚያስደንቅ ፍሬ አያዝልም። 17Id., Vol. 5, pp. 596, 597.AHAmh 239.2

    ዓይናቸውን በጨው ያጠቡ ብዙ ወይዛዝርት፤ ኃፍረታቸውን የተዉ ደፋር ሴቶች አሉ። እነዚህ ሴቶች እይታ ውስጥ ለመግባት የሚጠቀሙበት የማታለያ ኃይል አላቸው። በወጣት ወንዶች መካከል በመመላለስ ትኩረታቸውን ለማግኘት በመሽኮርመም የሚያጠምዱ፤ ከአገቡም ሆነ ካላገቡ ወንዶች ጋር መዳራትን የሚጋብዙ ሴቶች አሉ። ፊታችሁ ወደ ክርስቶስ ካልዞረና እንደ ብረት የጠነከራችሁ ካልሆናችሁ በሰይጣን መረብ ውስጥ መግባታችሁ አይቀሬ ነው። 18Medical Ministry, p. 147.AHAmh 239.3

    እላንት እውነትን የምትመሰክሩ ሆይ! ከተበላሸ ነገር በፍጥነት ትወጡ ዘንድ የተበከለ ሐሳብ ከሚተነፍሱ ጉዳቶች ትሸሹ ዘንድ እንደ እግዚአብሔር አምባሳደርነቴ እለምናችኋለሁ። እነዚህ የሚያረክሱት ኃጢአቶች ወደር በሌለው ጥላቻ ያንገሽግሿችሁ። በንግግር እንኳ አዕምሮአችሁ በእንደዚህ ዓይነት መንገድ እንዲመላለስ ከሚያደርጓችሁ አምልጡ፤ “ልብም የሞላውን አፍ ይናገራልና።”…..AHAmh 239.4

    ለተበላሸና ድብቅ አጀንዳ ላለው አስተያየት አንድ ሰከንድም እንኳ ቦታ እንዳትሰጡ። የቆሸሸ ወራጅ ውኃ የሚያልፍበትን አካባቢ ሁሉ አንደሚበክል ይህም ነፍስን ያጎድፋል። 19Testimonies for the Church, Vol. 5, pp. 146, 147.AHAmh 239.5

    ድንግልናውን ያልጠበቀ ቃል ወይም ፍንጭ በእርስዋ ፊት እንዲነገር የምትፈቅድ ሴት እግዚአብሔር አንደሚፈልጋት እየተመላለሰች አይደለችም። ተገቢ ያልሆነ ቅርርብን እንዲሁም ያልነጠረ አስተያየትን የምትፈቅድ እርስዋ እግዚአብሔር መሰል ሴትነትዋን የምትጠብቅ አይደለችም። 20Manuscript 4a, 1885.AHAmh 239.6

    በንፁህና በቅዱስ ክበብ የሚጠበቅ፦ እህቶቻችን እውነተኛ የዋህነትን ማበረታታት ይጠበቅባቸዋል። ዓይን አውጣዎች ወሬኞችና ስድ-አደጎች መሆን የለባቸውም፤ እዩኝ እዩኝ የማይሉ ትሁቶችና ለመናገር የዘገዩ እንጂ። የትህትና ተግባርን የሚያበረታቱ ይሁኑ። ቸር፣ ገራም፣ አዛኝ፣ ይቅር-ባይና የዋህ መሆን እግዚአብሔር የሚወዳቸውና የሚያስደስቱት ባህርያት ናቸው። ሴቶች ይህንን ደረጃ ከያዙ በቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉ ወይም በውጭ ወንዶች አላስፈላጊ በሆነ ትኩረት የሚጨናነቁ አይሆኑም፤ እነዚህ ሴቶች ፈሪሃ-እግዚአብሔር ያላቸውና በቅዱስ ንጽህና የተከበቡ እንደሆኑ ሁሉም ያውቃል። ይህም ዋስትና ከሌለው ነፃነት ይከልላቸዋል።AHAmh 240.1

    በአንዳንድ እግዚአብሔርን ስለመምሰል በሚመሰክሩ ሴቶች ዘንድ ወደ ጥፋትና ክፋት የሚመራ ግድ-የለሽና ልቅ የሆነ ነፃነት ያለው ባህርይ ይታያል። ሐሳባቸውንና ልባቸውን ሕይወትን በሚያጠሩ መልእክቶች በመሙላት የሚመሰጡ፤ እግዚአብሔርን የሚመስሉ፤ ነፍስ ከጌታ ጋር እንድትሆን ከፍ ከፍ የሚያደርጓት ሴቶች ግን ከታማኝነትና ከጨዋነት መንገድ በቀላሉ ፈቀቅ የሚሉ አይደሉም። እንደነዚህ ያሉ ሴቶች ከሰይጣን ሽንገላ በተጠናከረ ምሽግ የተከለሉ ናቸው፤ አታላይ ጥበቡን ለመቋቋም የተዘጋጁ ናቸው። 21 Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 456.AHAmh 240.2

    እንደ ክርስቶስ ተከታይነታችሁ በምሥጉን ሞያ የምትሳተፉ ሆይ ውድና ዋጋ ለማይገኝለት የቁጥብነት የከበረ ማንነታችሁ ከፍተኛ ዋጋ እንድትሰጡ እለምናችኋለሁ፤ ይህ የጨዋነት ባህርይን ያስጠብቃል። 22Id., p. 458.AHAmh 240.3

    ሐሳባችሁን ተቆጣጠሩት፦ ሐሳባችሁን መቆጣጠር መቻል አለባችሁ። ይህን ማድረግ ቀላል አይደለም፤ ያለ ቅርብ ክትትል እንዲያውም ያለ ከባድ ጥረት ልታሳኩት አትችሉም። ሆኖም እግዚአብሔር ይህንን እንድታደርጉት ይጠብቅባችኋል። በእያንዳንዱ ተጠያቂ ፍጡር ላይ ያረፈ ግዴታ ነው። በአስተሳሰባችሁ ለእግዚአብሔር ተጠያቂዎች ናችሁ። በጎደፉ ጉዳዮች ላይ ሐሳባችሁ እንዲኖር ፈቅዳችሁ ለከንቱ ምናብ የምትገዙ ከሆነ ሐሳባችሁን ወደ ተግባር ብትቀይሩት ጥፋተኞች የምትሆኑትን ያህል በእግዚአብሔር ፊት በደለኞች ናችሁ። ድርጊቱን ከመፈፀም የሚከለክለው እድል አለመገኘቱ ነው። የቀን ተሌት ቅዠትና የሐሳብ ሕንፃ ግንባታ መጥፎና እጅግ አደገኛ ልማዶች ናቸው። እነዚህ ልማዶች አንድ ጊዜ መሠረት ከጣሉ በኋላ ለመስበርና ሐሳብን ንጹህ፣ ቅዱስና ከፍ ከፍ ወዳለው ርዕስ ለመመለስ ፈጽሞ የማይቻል ነው ማለት ይቀላል። 23Id., p. 561.AHAmh 240.4

    ከሽንገላ ተጠንቀቁ፦ ወንዶች ሲሞገሱ፣ ሲሸነጋገሉና በከንቱ ውዳሴ ሲደለሉ ማየት ያሳምመኛል። እንደዚህ ዓይነቱን ትኩረት የሚቀበሉ አንዳንዶቹ የእርሱን ስም በከንፈራቸው ሊሸከሙ የተገባቸው ያለመሆናቸውን ሐቅ እግዚአብሔር ገልጾልኛል። ውጫዊ መልክን በሚመለከቱ ውስን በሆኑት ፍጡራን ግን ከፍ ከፍ ተደርገው ሰማይ ይነካሉ። እህቶቼ ሆይ እነዚህን ችግር የበዛባቸው ወዳቂና ተሳሳች ወጣቶችም ሆኑ ሽማግሌዎች ያገቡም ሆኑ ያላገቡ ወንዶች እየደባበሳችሁ ከእውነት በራቀ ውዳሴ አታሞግሷቸው። ያለባቸውን ድክመቶች አታውቁም እንጂ የምትለግሷቸው ትኩረቶች እነዚህ የምትቸሯቸው ከመጠን ያለፉ ምሥጋናዎች መጥፋታቸውን የሚያረጋግጡ ሊሆኑ ይችላሉ። በዚህ ረገድ ያለው የሐሳብ ውስንነት አርቆ ማየት ያለመቻልና የጥበብ ጉድለት ያሳስበኛል።AHAmh 240.5

    የእግዚአብሔርን ሥራ የሚሠሩ ክርስቶስ በልባቸው የሚኖር ወንዶች፣ የግብረገብነትን ደረጃ ይህን ያህል ዝቅ አያደርጉትም፤ ከፍ ከፍ ሊያደርጉት ሁልጊዜም ይተጋሉ አንጂ። በሴቶች ሽንገላና ዳበሳ ደስታ የሚያገኙ አይደሉም። ያገቡም ሆነ ያላገቡ ወንዶች እንዲህ ይበሉ “አትንኩኝ! መልካሙ ነገር በክፉ አንዲነገር፣ ለተዋረደ ትዕይንት ራሴን አሳልፌ አልሰጥም። የእኔ መልካም ስም ከወርቅና ከብር የበለጠ ዋጋ ያለው ሀብቴ ነው፤ ሳይወይብና ሳይጎድፍ እጠብቀዋለሁ። ሰዎች ያንን ስሜን ቢያጠፉ [በራሳቸው የጎደፈ ማንነት ምክንያት] የማያቋርጥ ዘለፋ ስለሆነባቸው የባህርይውን ንጽህናና ቅድስና ጠልተው ክርስቶስን በክፉ እንዳነሱት ሁሉ እኔንም ይወቅሳሉ እንጂ ሊኮንኑኝ የሚያስችላቸው ምክንያት ሰለሰጠኋቸው አይሆንም።” 24Id., Vol. 5, p. 595.AHAmh 241.1

    አገልጋዩ የሚገፋፋ ከሆነ፦ እጅግ ቀላል የሚባለው የስሜት ጫና ምንጩ ከየትም ይሁን ለኃጢአት እንድትገዢ የሚጋብዝሽ ከሆነ ወይም ውስንም ቢሆን ከእያንዳንዱ ሰው ጋር ያለሽ አግባብነት የሌለው ነፃነትሽ የሚንፀባረቅ ከሆነ፣ ለተከበረው ሴትነትሽ እጅግ የከፋው ስድብ እንደሆነ ሊሰማሽ ይገባል። አግባብነት በሌለው ጊዜና ቦታ ጉንጭሽ ላይ ስትሳሚ የሰይጣንን መልእክተኛ በመቃወም ድርጊቱ ሊያስፀይፍሽ ይገባል። ይህ የተፈጸመው ድርጊት ከፍተኛ ቦታ ከያዘ በቅዱስ ነገሮች ላይ ከሚሠራ ሰው ከሆነማ፣ ጭራሽ የኃጢአቱ መጠን አሥር እጥፍ ከባድ በመሆኑ ፈሪሃእግዚአብሔር ያላትን ሴት ወይም ወጣት በታላቅ ድንጋጤ ወደ ኋላ እንድታፈገፍግ ሊያደርጋት ይገባል። የምትሸሹት እንድትፈጽሙት ከሚገፋፋችሁ ኃጢአት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር አገልጋይ ከመሆኑ የተነሣ ሰዎች ከሚያከብሩት ነገር ግን ግብዝነትና ክፉነት ከተላበሰው ማንነቱ ጭምር ነው። 25Id., Vol. 2, pp. 458, 459.AHAmh 241.2

    የወንጌል መልእክተኛው የተዋረዱትን ፍላጎቶቹን መቆጣጠር ካልቻለ፤ የሐዋርያውን ዱካ መከተል ተስኖት ኃጢአትን በስሙ መጥራት አልሆንለት ብሎ ምሥክርነቱንና እምነቱን የሚያረክስ ከሆነ፤ የሚፈጽመው ሰው የእግዚአብሔር አገልጋይ በመሆኑ ብቻ ኃጢአት ወይም ወንጀል ጥፋት ከመሆን ስለማይዘል፣ የአድቬንቲስት ቤት እግዚአብሔርን ስለመምሰል የሚናገሩ እህቶቻችን ለቅጽበትም ቢሆን እራሳቸውን እንዳያታልሉ። በኃላፊነት የተቀመጡ ሰዎች ከኃጢአት ጋር ያላቸው ቅርርቦሽ የኃጢአቱን ግዝፈት ወይም አስከፊነት በማንም አዕምሮ ሊቀንሰው አይገባም። ኃጢአት በትክክለኛው ኃጢአትነቱና አስፀያፊነቱ ሊታይ፣ ከጥንት ጀምሮ እንደነበረው ገጽታው ሊስተዋል ይገባዋል። ንጹህና ከፍ ከፍ ያለ ሕሊና ያላቸው ለኃጢአት ተገዢ ከሆነው ከእርሱ መርዙ ገዳይ ከሆነ እባብ በድንጋጤ እንደሚሸሹ ሁሉ ሊርቁትና ሊፀየፉት ይገባቸዋል። እህቶቻችን ከፍ ከፍ ያሉና የልብ ንጽህና ያላቸው ቢሆኑ ማንኛውም ብልሹ እንቅስቃሴ ከአገልጋዩም ቢሆን እንኳ ፈጽሞ እንዳይደገም በሚያደርግ ግልጽ ተቃውሞ፣ ሁለተኛ እንዳይሞከር በሚያስገድደው ሁኔታ ሊገፈተር ይችላል። 26Id., p. 457.AHAmh 241.3

    ለጋብቻ ቃል-ኪዳናችሁ ታማኞች ሁኑ፦ ለጋብቻው የገባውን ቃል ኪዳን ለመጠበቅ ባልና አባት እንዴት ጥንቁቅ መሆን አለበት! ለወጣት ሴቶች ወይም ላገቡት ሴቶች ጭምር እንደ ከፍተኛውና ቅዱሱ ደረጃ - የእግዚአብሔር ትዕዛዝ - በማይራመዱ ሁሉ ሐሳቡ እንዳይነሳሣ እንዴት ጥንቁቅ መሆን አለበት! AHAmh 242.1

    እነዚያ ትዕዛዛት የልብ ሐሳብን፣ ፍላጎትንና ዓላማን የሚደርሱ እጅግ ወሰነ-ሰፊ እንደሆኑ ክርስቶስ ያሳያል። ብዙዎች ጥፋተኛ የሚሆኑት እዚህ ላይ ነው። የልባቸው ሐሳብ እግዚአብሔር እንደሚፈልገው ንጹህና ቅዱስ መልክ የለውም። ጥሪያቸው የከበረ፣ መክሊታቸው የነጠረ ቢሆንም ቅሉ እግዚአብሔር ኃጢአታቸውን ልብ ይላል፤ ትንሽ ችሎታ፣ ትንሽ ብርሃንና ዝቅተኛ ተጽዕኖ ካላቸው ሰዎች የበለጠ ከቁጣው ጽዋ ይጠጡ ዘንድ ለይቶ ይቆጥራቸዋል። 27Id., Vol. 5, pp. 594, 595.AHAmh 242.2

    ላገቡ ወንዶች እንድናገር ታዝዣለሁ፤ አክብሮታችሁና መውደዳችሁ የተገባቸው ሚስቶቻችሁ - የልጆቻችሁ እናቶች ናቸው። ትኩረታችሁ ለእነርሱ የተሰጠ፣ ሐሳባችሁ ለእነርሱ ደስታ በመፍጠር ላይ የሚያውጠነጥን ሊሆን የተገባው ነው። 28Letter 231, 1903.AHAmh 242.3

    የክርስቶስ ተከታይ የሆነ ሁሉ የሚያንፀባርቀውን ሞገስ የተላበሰውን፣ እግዚአብሔርን መሳይ ጎልማሳነት ያልጠበቀ ባልና አባት ያለባቸው ቤተሰቦች እንዳይ ተደርጌአለሁ። በሕይወት እስካሉ ድረስ ሊያፈቅራት ሊያከብራትና ከፍ ከፍ ሊያደርጋት በእግዚአብሔርና በመላእክቱ ፊት የገባውን ቃል ጥሶ፣ ሚስቱ የተገባትን የቸርነት የየዋህነትና የደግነት ተግባሩን መፈፀም አልቻለም። የቤት ሥራ እንድትሠራ የተቀጠረችው ወጣት በነፃነት ጸጉሩን እንድታስተካክልለትና የተለየ ትኩረት እንድትሰጠው በመፍቀድ ሐሴት ያደርጋል፤ በቂልነቱ ይደሰታል። ለሚስቱ ያለው ፍቅርና ትኩረት ድሮ እንደነበረው አይደለም፤ ተግባራዊነቱ ቀንሷል። ሰይጣን በዚህ ቦታ እየሠራ እንደሆነ እርግጠኞች ሁኑ። ለቀጠራችኋት ረዳታችሁ ክብር ስጡ፤ አሳቢና ቸር ሁኑላት፤ ነገር ግን እዚያ ላይ አቁሙ። ጠበቅ ወዳለ መላመድ የሚመራችሁን የአድቬንቲስት ቤት ግቱት። 29Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 461.AHAmh 242.4

    የቤተሰብን ምስጢር ጠብቁ፦ ንጽህናቸውንና ቅድስናቸውን ለመጠበቅ በማሰብ የእያንዳንዱን ቤተሰብ ግላዊነት ለመከለል በዙሪያቸው የገነቡአቸው ቅጥሮች በመፍረሳቸው ምክንያት የስንቶች ሕይወት መራራ ሆኗል! ሦስተኛ ወገን የሚስትን አመኔታ በማግኘት የቤተሰቡ ገመናዎች ለዚህ ልዩ ጓደኛ ፍንትው ብለው በፊቱ ይቀርቡለታል። ይህ ባልና ሚስትን ለመለያየት የሚጠቀምበት የሰይጣን መሳሪያ ነው። ኦ! ይህ ነገር መቆም ቢችል ዓለም ከምን ዓይነት ችግር ይተርፍ ነበር! ለእርስ በርሳቸሁ ጉድለት ያላችሁን ማስተዋል በራሳችሁ ልብ ውስጥ ቆልፉበት። ችግሮቻችሁን ለእግዚአብሔር ብቻ ንገሩ። ንጹህ በውስጡ መራራነት የሌለውና የሚያጽናና ትክክለኛ ምክር እርሱ ይሰጣችኋል። 30Id., p. 462.AHAmh 243.1

    ሚስት የቤተሰቧን ችግሮች ስታወሳ ወይም ባልዋን በሌላ ወንድ ፊት ስታማርር የጋብቻ ቃል-ኪዳንዋን እያፈረሰች ነው፤ የትዳር ግንኙነታቸውን ቅድስና የሚጠብቀውን ቅጥር በማፍረስ ባልዋን ታዋርደዋለች፤ በርዋን ቦርቀቅ አድርጋ በመክፈት ሰይጣን ከነተንኮለኛ ፈተናዎቹ ጋር ዘው ብሎ እንዲገባ ትጋብዘዋለች። ይህ ሰይጣን ሁሌም የሚመኘው ነገር ነው። አንዲት ሴት ሐዘንዋን ቅሬታዎችዋንና ፈተናዎችዋን ይዛ ወደ ክርስርቲያን ወንድም ብትመጣ እንዲህ ይምከራት፡- ችግሮችዋን ለሌላ ማዋየት ካለባት ምስጢረኛ የሚሆንዋት እህቶችን ትምረጥ። እንዲህም ሲሆን ጥፋት ሳይታይና የእግዚአብሔር ጉዳይ የወቀሳ ሃፍረት ሳይደርስበት ነገሩ እልባት ያገኛል። 31Id., p. 306.AHAmh 243.2

    መንገድ ከመሳት እንዴት መጠበቅ እንደሚቻል፦ ለሕዝባችን እንዲህ ብዬ እናገራለሁ፤ #ወደ የሱስ ብትጠጉና የእምነታችሁን ቃል-ኪዳን ሥርዓት ባለው ሕይወትና እግዚአብሔራዊ ንግግር ብታስውቡት፣ እግሮቻችሁ የተከለከሉትን መንገዶች ለመርገጥ ከመሳት ይቆማሉ። በጸሎት ብቻ፤ ሁልጊዜ በጸሎት ብትመለከቱ እግዚአብሔር በመካከላችሁ እንዳለ አድርጋችሁ ሁሉንም ነገራችሁን ብታከናውኑ፣ ለፈተና እጅ ከመስጠት ትተርፋላችሁ፤ ያልጎደፈ ነውር የሌለበትና ንጹህ ሆናችሁ እስከመጨረሻው ልትዘልቁ ተስፋ ይኖራችኋል። የመተማመናችሁን መጀመሪያ እስከ መጨረሻው አጥብቃችሁ ከያዛችሁ መንገዳችሁ በእግዚአብሔር የተደላደለ ይሆናል። ፀጋ የጀመረውን ሥራ በጌታችን መንግሥት የክብር ዘውድ ይጭንበታል። የመንፈስ ፍሬዎች ፍቅር፣ ደስታ፣ ሠላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ ሃይማኖት፣ ገርነት፣ መሻትንም መግዛት ናቸው። እነዚህን የሚቃወም ሕግ የለም። ክርስቶስ በእኛ ውስጥ ቢኖር ሥጋን ከምኞቱና ከሐሳቡ ጋር በመስቀል እንቸነክረዋለን።;32Id., Vol. 5, p. 148.AHAmh 243.3

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents