Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

የአድቬንቲስት ቤት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First

    ምዕራፍ ሃያ አራት—የቤተሰብ መጠን

    ለእናቶች፣ ለልጆችና ለማህበረሰቡ አደገኛ የሆነ ስህተት፦ ብዙ አባላት ያሉት ቤተሰብ ማስተዳደር መቻል አለመቻላቸውን በአግባቡ ሳያጤኑ፣ መመሪያና እንክብካቤ በመቀበል ረገድ በእነርሱ ላይ ሙሉ በሙሉ ጥገኛ በሆኑና እራሳቸውን መርዳት በማይችሉ ትናንሽ ፍጡራን ቤታቸውን የሚሞሉ ሰዎች አሉ። ይህ ለእናትየዋ ብቻ ሳይሆን ለልጆችና ለማህበረሰቡም ከባድ ጥፋት ነው…. ወላጆች ሁልጊዜ የልጆቻቸውን የወደፊት ህልውና ሊያስቡበት ይገባል። ለመኖር አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች ለማቅረብ ሲሮጡ፣ ያላቸውን ጊዜ ሁሉ ተጠቅመው ሲማስኑ በአድካሚ ሥራዎች ብቻ ተጠምደው ዕድሜያቸው እንዲያልቅ ሊገደዱ አይገባም።1Review and Herald, June 24, 1890.AHAmh 108.1

    የቤተሰባቸውን ቁጥር ከመጨመራቸው በፊት ልጆችን ወደዚህ ዓለም በማምጣታቸው እግዚአብሔር ሊከብር ወይስ ሊዋረድ እንደሚችል ማሰብ ይገባቸዋል። ከመጀመሪያው ጥምረታቸው ሰዓት ጀምሮ በእያንዳንዱ የትዳር ሕይወት ዓመታት እግዚአብሔርን ለማክበር መጣር አለባቸው።2Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 380.AHAmh 108.2

    የእናቲቱ ጤናማነት አስፈላጊ ነው፦ በወላጆች ላይ ከሚወድቀው ኃላፊነት የተነሣ ልጆችን መውለድ ከቤተሰቡ ደህንነት አንጻር አስፈላጊ መሆኑን በጥንቃቄ መመርመር ያስፈልጋል። እናት ልጆችዋን ለመንከባከብ በቂ ጉልበት አላት? አባት ልጁን በትክክለኛ መንገድ ለመቅረጽና ለማስተማር የሚችል ነው? የልጁ ዕጣ ፈንታ እንዴት ከግምት አይገባም! የስሜት ማርካት ፍላጎት ብቻ ገዝፎ ሸክሙ በሚስትና በእናት ላይ ይጫናል፤ ይህም ሕይወትዋን የሚያመነምን፣ መንፈሳዊ ጉልበትዋን ሽባ የሚያደርግ ይሆናል። በተቃወሰ ጤንነትና በቆረቆዘ መንፈስ እንደሚገባት መንከባከብ በማትችለው ትንሽ መንጋ ተከብባ ራስዋን ታገኘዋለች። ሊሰጣቸው የሚገባቸውን መመሪያ በማጣታቸው እግዚዘብሔርን በማዋረድ ያድጋሉ፤ እርጉም የሆነውን የራሳቸውን ተፈጥሮ ለሌሎች ያካፍላሉ፤ በመሆኑም ሰይጣን እንደፈለገ የሚያሽከረክረው ጭፍራ ይመሠርታሉ።3Review and Herald, Oct. 25, 1892.AHAmh 108.3

    ሌሎች ሊጤኑ የሚገባቸው ነገሮች፦ እግዚአብሔር ወላጆች አስተዋይ አዕምሮ እንዳላቸው ፍጡራን እንዲንቀሳቀሱ ይፈልጋል። ኑሮአቸውም ልጆች ሥነሥርዓት ሊማሩበት የሚችሉበት፤ እናት ታናናሾቹን ልጆችዋን ልትቀጣና ልታስተካክል የምትችልበትን አዕምሮአዊ ጉልበት ለመጠቀም ወኔና ጊዜ ያላት፤ ከመላእክት ጋር ህብረት የሚፈጥሩ ልጆችን ማሳደግ የምትችልበት ይሁን። በጨዋነት የድርሻዋን ሥራ በእግዚአብሔር ፍርሃትና ፍቅር ትሠራ ዘንድ ልጆችዋም ለቤተሰቡና ለህብረተሰቡ በረከት ይሆኑ ዘንድ ብርታት ሊኖራት ይገባል።AHAmh 108.4

    ባለቤቱና የልጆቹ እናት ከአቅምዋ በላይ በመሸከም በተስፋ መቁረጥ እንዳትሸነፍ፣ እነዚህን ነገሮች ሁሉ ባል በጥንቃቄ መመርመር አለበት። የልጆቹ እናት በቁጥር በርካታ የሆኑትን ህፃናት በሥነ-ሥርዓት ማሳደግ የሚሳናት፣ ልጆችዋንም በተገቢው ሥልጠና ልትገራ የማትችልበት ሁኔታ ላይ መሆንዋን በአንክሮ በመከታተል ሊያረጋግጥ ይገባዋል።4Review and Herald, June 24, 1890.AHAmh 109.1

    ለልጆቻቸው እንክብካቤና ትምህርት መስጠት ከሚችሉበት ፍጥነት ባለፈ ወላጆች ተጨማሪ ልጆች ሊያክሉ አይገባቸውም። በዓመት በዓመት እናት ህፃን ልጅ ማቀፏ ትልቅ ግፍ ነው። የአብሮነት ደስታን ይቀንሳል፤ ያጠፋልም፤ የቤት ውስጥ ሕይወትንም እንኩቶ ያደርገዋል። ልጆቻቸው ሊያገኙት የሚገባቸውን ጥንቃቄ ትምህርትና ደስታ ያሳጣል። ወላጆቻቸው ልጆቻችን ሊያገኙት ይገባል የሚሉትን እንክብካቤ ይነፍጋል።5Solemn Appeal, pp. 110, 111.AHAmh 109.2

    ምክር ብዙ ቤተሰብ ላላቸው ወላጆች፦ መልስ ሊያገኝ የሚገባው ጥያቄ:- “ልጆችን የማሳድገው የጨለማ ኃይላትን ለማብዛት፣ ለማጠናከርና ተጽዕኖአቸውን ለማጎልበት ነው ወይስ ለክርስቶስ ነው?” የሚለው ነው። የእግዚአብሔርን ጥያቄ የሚያሟሉ ይሆኑ ዘንድ ባህርያቸውን መቅረጽና በሥነሥርዓት ማስተዳደር የማትችሉ ከሆነ፣ ግድፈት ካለበት የማሠልጠን ችሎታችሁ የሚሰቃዩት ልጆች ጥቂት ቢሆኑ ለእናንተም ሆነ ለማህበረሰቡ ይሻላል። ልጆች ከህፃንነታቸው ጀምሮ ብልህ፣ አመዛዛኝና አዋቂ በሆነችው እናታቸው ተቀጥተውና ሠልጥነው፤ የጽድቅን ደረጃ በሚያሟላ ባህርይ በፈሪሃ-እግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር ሆነው ማደግ የማይችሉ ከሆነ የቤተሰባችሁን ቁጥር መጨመሩ ኃጢአት ነው። እግዚአብሔር በቂ ምክንያት ሰጥቷችኋል፤ እንድትጠቀሙበት ይጠይቃችኋል።6Testimonies for the Church, Vol. 5, pp. 323, 324.AHAmh 109.3

    እናቶችና አባቶች፣ ልጆቻችሁን ለልዑል እግዚአብሔር ማዘጋጀት የሚያስችል ዕውቀት እንደሌላችሁ ስታውቁ ለምን ትምህርት አትወስዱም? የሰይጣንን የማዕረግ ደረጃ ለማስፋት ለምን ልጆችን ወደዚህ ዓለም ታመጣላችሁ? በዚህ ትዕይንት እግዚአብሔር ደስ ይሰኛልን? ብዙ ቁጥር ያለው ቤተሰብ ሀብታችሁን እንደሚያንጎዳጉደው ስታወቁ፤ እናትየዋ እጇ በልጅ እንዲሞላና እያንዳንዷ ወላጅ ማድረግ የሚገባትን ሥራ ለመሥራት የሚያስችላት በመውለድ መካከል ያለው የዕረፍቷ ጊዜ እንደጠበበ ስታዩ፤ ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት እንዴት ይሳናችኋል? እያንዳንዱ ልጅ በእናትየዋ ጥንካሬ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ አለው፤ በዚህ ረገድ ወላጆች ጭንቅላታቸውን የማይጠቀሙ ከሆነ ልጆቻቸው በሥነ-ሥርዓት ያድጉ ዘንድ የሚያስችላቸው ምን እድል አለ? ወላጆች ይህንን ጉዳይ ከወደፊቱ ዘለዓለማዊ የአድቬንቲስት ቤት እውነታዎች ጋር በማነፃጸር በአንክሮ ያስቡት ዘንድ እንደሚገባ ጌታ እየተናገራቸው ነው።7Letter 107, 1898AHAmh 109.4

    የምጣኔ ሀብት ሁኔታዎች፦ ምን ምን ሁኔታዎች ለልጆቻቸው ሊመቻቹላቸው እንደሚችሉ ወላጆች በተረጋጋ መንፈስ ሊመረምሩት ይገባል። የሌሎች ሸክም ይሆኑ ዘንድ ልጆችን ወደዚህ ዓለም የማምጣት መብት የላቸውም። የሌሎች ዕዳ እንዳይሆኑ ቤተሰባቸውን ሊያስተዳድሩበት የሚችሉበት አስተማማኝ ሥራ አላቸው? ይህ ዓይነቱ ጥሪት በበቂ ሁኔታ ከሌላቸው መልካም እንክብካቤ፣ ምግብና ልብስ በማጣት የሚሰቃዩትን ልጆች ወደዚህ ዓለም በማምጣታቸው ወንጀል ይፈጽማሉ።8Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 380.AHAmh 110.1

    የንግድ ሥራ ጥበብ እጅጉን የሚጎድላቸው፣ በዚህ ዓለም ከሌሎች ጋር ተግባብተው መኖር የሚሳናቸውና ሥልጠናውም የሌላቸው ሰዎች ናቸው በአብዛኛው ቤታቸውን በልጅ የሚሞሉት። በአንፃሩ ደግሞ ሀብት ለማፍራት ችሎታ ያላቸው ሰዎች በሥርዓት ማሳደግ ከሚችሉት በላይ ልጆች አይወልዱም። እራሳቸውን መርዳት የማይችሉ እነርሱ ልጆች ሊኖሯቸው አይገባም።9Solemn Appeal, p. 103.AHAmh 110.2

    ግራ መጋባት አንዳንድ ጊዜ ወደ ቤተ-ክርስቲያን እንዴት እንደሚመጣ፦ ብዙዎች ብቻቸውን እያሉ ለመኖር የሚያጣጥሩ፣ ሊያስተዳድሩበት የሚችሉት ምንም ጥሪት እንደሌላቸው እያወቁ፣ አግብተው ቤተሰብ መመሥረት ይመርጣሉ። ከዚህም ይባስ ብሎ ደግሞ ቤተሰብ የማስተዳደር ችሎታም የላቸውም። ድሮ ወላጆቻቸው ቤት ውስጥ የነበራቸው ቆይታ በልቅነትና በቸልተኝነት ልማድ የታወቀ ነበር። እራሳቸውን መቆጣጠር የማይችሉ፣ ስሜታዊ፣ ትዕግሥት-የለሽና ተጨናናቂ ናቸው። እንደዚህ ዓይነት ሰዎች መልእክቱን ሲቀበሉ በሀብታም የቤተ-ክርስቲያን ወንድሞቻቸው እርዳታ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ይሰማቸዋል። የጠበቁትንም ማግኘት ሲሳናቸው በቤተ-ክርስቲያን ላይ በማጉረምረም አባላቱ እምነታቸውን እየኖሩት እንዳልሆነ ይወነጅሏቸዋል። በዚህ ጉዳይ መሰቃየት ያለበት ማን ነው? የእነዚህን ሰፊ የድኃ ቤተሰቦች ለመንከባከብ ሲባል የእግዚአብሔር ጉዳይ መሠረቱ ይናጋ? በተለያዩ ቤተ-ክርስቲያናት ያሉ ጎተራዎች ይራቆቱ? አይደለም። መሰቃየት ያለባቸው ወላጆቹ ናቸው። ሰንበትን በማክበራቸው ምክንያት በፊት ከነበረባቸው እጦት የባሰ ችግር አይገጥማቸውም።10Testimonies for the Church, Vol. 1, p. 273.AHAmh 110.3

    ሚሲዮናዊ አገልግሎት እንዴት ውስን ሊሆን እንደሚችል፦ አገልጋዮች ወደ ሩቅ አገራት ሄደው እንዲያገለግሉ በሚመረጡበት ጊዜ መቆጠብ የሚችሉ፣ ብዙ ቤተሰብ የሌላቸው፣ የጊዜን ውስንነትና ሊሠራ ያለውን ታላቅ ሥራ የሚገነዘቡ፤ እጃቸውንና ቤታቸውን በልጅ የማይሞሉ፤ ከአንዱና ከታላቁ ሥራ ሀሳባቸውን ሊያደናቅፍ ከሚችል ነገር ሁሉ በቻሉት መጠን ራሳቸውን ነፃ የሚያደርጉ ሰዎች መመረጥ አለባቸው። ሚስትም የተሰጠች ከሆነችና ነፃ መሆን ከቻለች ከባልዋ ጎን በመቆም ከርሱ እኩል ማከናወን ትችላለች። ብዙ ሴቶችና ወንዶች ልጆችን ለእግዚአብሔር በማበርከት ለክብሩ በሚጠቀምበት የተለየ ስጦታ እግዚአብሔር ሴቶችን ባርኳቸዋል። ሆኖም ብዙ ሥራ ሊሠሩለት የሚችሉ ብቃት ያላቸው ሴቶች ልጆቻቸውን ለመንከባከብ ሲሉ እቤት ታጉረው ቀርተዋል። AHAmh 110.4

    ‘አገልጋይ’ የሚለውን ቃል ሙሉ በሙሉ የሚወክሉ ሠራተኞች ያስፈልጉናል። ራስወዳድ ጉዳያቸውን ወደ ጎን ትተው የእግዚአብሔርን ነገር የሚያስቀድሙ፤ ዓይናቸው ለእርሱ ክብር ብቻ የተገለጠ፤ ወደሚያዝዛቸው ቦታ ሁሉ ለመሄድ በተጠንቀቅ የቆሙ፤ በየትኛውም የሥራ መስክ የእውነትን እውቀት ለማሰራጨት የሚሠሩ አገልጋዮች ያስፈልጉናል። እግዚአብሔርን የሚወድዱና የሚፈሩ በመስክ ሥራም የሚያግዙ ሚስቶች ያሏቸው ወንዶች እንፈልጋልን። ቤተሰብ ያላቸው ብዙ ሰዎች ለሥራ ይወጣሉ፤ ሆኖም ሙሉ ለሙሉ ለሥራው የተሰጡ አይሆኑም። ሀሳባቸው የተከፋፈለ ይሆናል። ለቤተሰቦቻቸው ሲሉ በቤታቸው አቅራቢያ ተወስነው መሥራት እንዳለባቸው ባይሰማቸው ኖሮ፣ ሊያካልሏቸው የሚችሏቸውን ብዙ እሩቅ ሥፍራዎች በሚስታቸውና በልጆቻቸው ሐሳብ ምክንያት ሳይገቡባቸው ይቀራሉ።11Review and Herald, Dec. 8, 1885.AHAmh 111.1