Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

የአድቬንቲስት ቤት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First

    ምዕራፍ አሥር—ምክር በሚያስፈልግበት ጊዜ

    ከመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ውሰዱ፦ ጋብቻ በእግዚአብሔር የተመሠረተና የተቀደሰ በመሆኑ በራስ-ወዳድነት መንፈስ ሊፈፀም አይገባም። ወደ ጋብቻ ለመግባት የሚያስቡ ሁሉ በጥንቃቄና በፀሎት አስፈላጊነቱን መመርመር አለባቸው። መለኮታዊ ምክሩንም በመጠየቅ እየተከተሉት ያሉት መንገድ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር የሚስማማ እንደሆነ በማወቅ እርግጠኛ መሆን ይገባቸዋል። በዚህ ረገድ የተሰጠው የእግዚአብሔር ቃል በጥንቃቄ መመርመር አለበት። በቃሉ በተሰጠው አቅጣጫ መሠረት በእውነተኛ ፍላጎት የሚመሠረት ትዳር ሰማይ በደስታ የሚመለከተው ነው።1Letter 17, 1896.AHAmh 42.1

    በሚያመዛዝን መንፈስና ስሜታዊ ባልሆነ አካሄድ ልንመረምረው የሚገባን ነገር ቢኖር የጋብቻ ጉዳይ ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር የሚያስፈልግ ከሆነ ሰዎች መመርመር ያለባቸው ዕድሜ-ልካቸውን የሚያጣምራቸው እርምጃ ከመጀመሩ በፊት ነው። በዚህ ዙሪያ የተለመደው አካሄድ ግን ስሜትን መከተል ነው። በአብዛኛው ፍቅር ያደከመው ስሜታዊነት መሪውን ይቆጣጠርና ለእርግጠኛ ጥፋት ይዳርጋቸዋል። ከሌላው ጉዳዮቻቸው ሁሉ ይልቅ ወጣቶች ጥበብ የሚጎድላቸውና የማያመዛዝኑት እዚህ ላይ ነው። የጋብቻ ነገር በእነርሱ ላይ የሚያደነዝዝ ኃይል ሆኖባቸዋል። እራሳቸውን ለእግዚአብሔር አያስረክቡም። ልክ በእቅዳቸው ሰው ጣልቃ እንዳይገባባቸው የሰጉ ይመስል ስሜታቸውን አፍነው ወደ ፊት በድብቅ ይራመዳሉ።2Fundamentals of Christian Education, p. 103.AHAmh 42.2

    ብዙዎች በአደገኛ የወደብ ዳርቻ እየቀዘፉ ናቸው፤ መሪ ያስፈልጋቸዋል። የራሳቸውን ጩኸት ለመከተል ብቁነት እየተሰማቸው በጣም አስፈላጊውን እርዳታ ያንቋሽሻሉ። እምነታቸውንና ደስታቸውን የሚያንኮታኩት የተደበቀ ቋጥኝ ሊገጫቸው እንደሆነ አያስተውሉም። የህያው ቃሉ ጥንቁቅ ተማሪ ካልሆኑ በስተቀር በዚህና በወደፊት ሕይወታቸው የራሳቸውንና የሌሎችን ደስታ የሚያውክ ከባድ ጥፋት ይሠራሉ።3Id., p. 100.AHAmh 42.3

    ፀሎት ለትክክለኛ ውሳኔ አስፈላጊ ነው፦ ሴቶችና ወንዶች መጋባት ከማሰባቸው በፊት በቀን ሁለት ጊዜ የመፀለይ ልምድ ከነበራቸው፤ ለመጋባት ባሰቡ ጊዜ በቀን አራት ጊዜ መፀለይ ይኖርባቸዋል። ትዳር በዚህና በሚመጣው ዓለም ሕይወት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድር፣ ሊጎዳም የሚችል ነው….AHAmh 42.4

    ብዙዎቹ የዚህ ዘመን ጋብቻዎችና የሚፈጸሙበት አኳኋን የመጨረሻዎቹ ቀናት ምልክቶች ናቸው። ወንዶችና ሴቶች መንቻካና ሐሳበ-ግትር ናቸው፤ እግዚአብሔርንም ጉዳያቸው ውስጥ አያስገቡትም። በዚህ የተቀደሰና አስፈላጊ ጉዳይ ምንም ሚና መጫወት የሌለበት ይመስል ኃይማኖታቸውን ወደ ጎን ይገፉታል።4Messages to Young People, p. 460.AHAmh 42.5

    ልብ የሚያጠፋ የፍቅር ስሜት ለምክር ጆሮ በማይሰጥበት ጊዜ፦ ሁለት ሰዎች ይላመዳሉ፤ ልብ በሚያቀልጥ የፍቅር ስሜት ውስጥ ይገባሉ፤ ትኩረታቸው በሙሉ ይወሰዳል። ማመዛዘን ይታወራል፤ ውሳኔውም ይገለበጣል። ምንም ዓይነት ምክር ወይም ቁጥጥር አይቀበሉም፤ ለሚመጣው መዘዝ ሳይጠነቀቁ የራሳቸውን ሐሳብ ብቻ ይከተላሉ። ልክ እንደ ወረርሽኝ የሚተላለፍ በሽታ የተጠናወታቸው ስሜታዊ ፍቅር ሥራውን ይሠራል - ምንም ሊያቆመው የሚችል ነገር እንደሌለ እስኪመስል ድረስ። እነዚህ ሰዎች በጋብቻ ቢጣመሩ ሕይወታቸው በሙሉ ደስታ የሌለበት መራራ እንደሚሆን የተገነዘቡ በዙሪያቸው ያሉ ሰዎች ይኖሩ ይሆናል። ልመናቸውና ልባዊ ምክራቸው ግን ከንቱ ይቀራል። ምን አልባትም በእንደዚህ ዓይነቱ ጥምረት ምክንያት እግዚአብሔር ሊባርከውና ሊቀድሰው የፈለገው የአንደኛው ወገን ጠቀሜታ ተሰናክሎና ወድሞ ይቀራል፤ ሆኖም የሌሎች ግንዛቤ የመፍጠር ጥረትና ግፊት ተቀባይነት ያጣል። ልምድ ባላቸው ወንዶችና ሴቶች የሚሰነዘረው ሐሳብ ሁሉ ውጤት ሳያመጣ ይቀራል፤ ፍላጎት-መር የሆነው ውሳኔአቸውን ለማጠፍ ጉልበትአልባ ይሆናል። ለጸሎት ስብሰባና ለማንኛውም ከኃይማኖት ጋር ለሚገናኝ ነገር ፍላጎት ያጣሉ። ለእርስ በእርሳቸው ካላቸው ስሜታዊ ፍቅር የተነሣ ለሕይወት ያለባቸውን ግዴታ እንደ ቀላል ነገር ይቆጥሩታል።5Review and Herald, Sept. 25, 1888.AHAmh 42.6

    ወጣቱ የዕድሜና የተሞክሮ ጥበብ ያስፈልገዋል፦ በጋብቻ ውስጥ ብዙ ስቃይ ሲያጋጥም እያየ ወጣቱ ብልሃተኛ የማይሆነው ለምንድን ነው? የበሰሉና በዕድሜ ልምድ ያላቸው ሰዎች ምክር አያስፈልገንም ማለቱን የገፋበት ለምንድን ነው? ብዙ ወንዶችና ሴቶች አንድ አስፈላጊ [የንግድ] ሥራ ከመጀመራቸው በፊት እራሳቸውን ያዘጋጃሉ፤ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋሉ። ውድቀት እንዳያጋጥማቸው ጊዜያቸውንና ገንዘባቸውን ሰውተው በጉዳዩ ላይ ጥንቃቄ የተሞላበት ጥናት ያደርጋሉ። ታዲያ የወደፊቱን ትውልድና የወደፊቱን ሕይወት ሊጎዳ ወደሚችል ግንኙነት - ወደ ትዳር - ሲገባ ምን ያህል የበለጠ ጥንቃቄም ማድረግ ያስፈልጋል? በተቃራኒው ግን ጋብቻ በቧልትና በፍሬ-ቢስ ጨዋታ፤ በስሜት ግፊትና ፍላጎት፤ በእውርነትና ባልተረጋጋ መንፈስ በጥልቀት ሳይጤን ይፈፀማል። ለዚህ ብቸኛው ማብራሪያ የሚሆነው ሰይጣን ነፍሳትን ለማጥመድ መረቡን በመዘርጋት የዚህን ዓለም ሰቆቃና ጥፋት ለማየት ተግቶ መሥራቱ ነው። እነዚህ አዙሮ ማየት የተሳናቸው ሰዎች የዚህን ዓለም ደስታና የሚመጣውን ዓለም ቤታቸውን በማጣታቸው ዲያብሎስ ሐሴት ያደርጋል።6Review and Herald, Feb. 2, 1886.AHAmh 43.1

    የወላጆች የበሰለ አስተያየት ዋጋ ሊሰጠው ይገባል፦ ልጆች ያለ ወላጆቻቸው ምክርና አስተያየት የራሳቸውን ፍላጎትና ዝንባሌ መከተል አለባቸው? አንዳንዶች ለወላጆቻቸው ምኞት ምርጫና የበሰለ አስተያየት ቁብ የሚሰጡ አይመስሉም። የልጅነት ፍቅርና እራስ-ወዳድነት ልባቸውን ዘግቶታል። በዚህ ረገድ የወጣቶች አዕምሮ ሊነቃቃ ይገባዋል። ከትዕዛዛቱ ውስጥ የተስፋ ቃል የተገባለት አምስተኛው ትዕዛዝ ብቻ ነው። ቀላል እንደሆነ ተደርጎ እንዲያውም አፍቃሪው በእርግጥ እያወቀው ቸል ይለዋል። የእናትን ፍቅር ማቃለል፣ የአባትንም እንክብካቤ መናቅ ተመዝግበው ያሉ የብዙ ወጣቶች ኃጢአቶች ናቸው። AHAmh 43.2

    ይህን ጉዳይ በተመለከተ እጅግ ከፍተኛ ስህተት ከሆኑት አንዱ በዕድሜ ያልበሰሉና ልምድ የሌላቸው ወጣቶች ፍቅራቸው ሊረበሽ አይገባም፤ በፍቅር ገጠመኞቻቸውም ጣልቃ መግባት አያስፈልግም የሚለው ነው። ከሁሉም አቅጣጫ ሊታይና ሊመረመር የሚገባው ጉዳይ ቢኖር ግን ይህ ነው። ከሌሎች ልምድ በሚያገኙት ድጋፍ በመታገዝ በተረጋጋ መንፈስና በጥንቃቄ ነገሮችን መመዘን ለሁለቱም ወገኖች በእርግጥ አስፈላጊ ነው። በአብዛኛው ሕዝብ ግን ይህ ጉዳይ እንደ ቀላል ነገር የሚታለፍ ነው። ወጣት ጓዶች ሆይ እግዚአብሔርንና ፈሪሃ-እግዚአብሔር ያላቸው ወላጆቻችሁን አማክሩ፤ በጉዳዩ ፀልዩበት።7Fundamentals of Christian Education, p. 104.AHAmh 44.1

    ለእግዚአብሔር ባደሩ ወላጆቻችሁ ተደገፉ፦ እግዚአብሔርን በሚፈሩ ወላጆች ተባርካችሁ ከሆነ ምክራቸውን ጠይቁ። ምኞታችሁንና እቅዳችሁን ንገሯቸው፤ ሕይወት ካካፈለቻቸው ልምድ ትምህርት ውሰዱ።8Ministry of Healing, p. 359.AHAmh 44.2

    ልጆች ከወላጆቻቸው ጋር በጣም የተቀራረቡ ቢሆኑ ቢተማመኑባቸውና የደስታና የሐዘን ሸክማቸውን በእነርሱ ላይ ቢያራግፉ ከብዙ የወደፊት የልብ ውጋት እራሳቸውን ይጠብቃሉ። የትኛው ትክክለኛ አካሄድ እንደሆነ ግራ ሲገባቸው እይታቸውን በወላጆቻቸው ፊት አቅርበው ምክራቸውን ይጠይቁ። ለእግዚአብሔር ታማኝ ከሆኑ ወላጆቻቸው የተሻለ ሊመጣ የሚችለውን አደጋ በጥንቃቄ መርምሮ ማን ሊያስረዳቸው ይችላል? ክርስቲያን ልጆች ፈሪሃ-እግዚአብሔር ያላቸውን የወላጆቻቸውን ፍቅርና ድጋፍ በዓለም ካለው በረከት ሁሉ በላይ የከበረ ስጦታ እንደሆነ አድርገው ያምናሉ። ወላጆች ልጆቻቸው ባዘኑ ጊዜ ያጽናኗቸዋል፤ እግዚአብሔር ይጠብቃቸውና ይመራቸው ዘንድ ይፀልዩላቸዋል። ከሁሉም በላይ ደግሞ ፈጽሞ ወደ ማይጥላቸው ጓደኛቸውና ጠበቃቸው ወደ ሆነው የሱስ ይመሯቸዋል።9Fundamentals of Christian Education, p. 105, 106.AHAmh 44.3

    ወላጆች የልጆቻቸውን ፍላጎት መልክ ማስያዝ አለባቸው፦ የሚስማማቸው አጋራቸው ጋር እንዲቆራኙ የወጣቶችን ፍላጎት በመምራት በኩል ወላጆች ኃላፊነት የተጣለባቸው መሆኑ ሊሰማቸው ይገባል። በመልካምና በዕውነት እንዲሳቡ አድርገው ገና ከልጅነታቸው ጀምረው ንጹህና ጨዋ እንዲሆኑ በእግዚአብሔር እርዳታ በማስተማርና ምሣሌ በመሆን የልጆቻቸውን ባህርይ መቅረጽ ወላጆች የእነርሱ ግዴታ መሆኑን መገንዘብ አለባቸው። መልካም መልካምን ይስባል፤ መልካም መልካምን ያደንቃል። የእውነት የንጽህናና የመልካምነት ፍቅር አስቀድሞ በነፍሳቸው ይተከል፤ ከዚያም ወጣቶች እነዚህ ባህርያትን ከያዙት ሌሎች መሰሎቻቸው ጋር ህብረት መፍጠርን ይሻሉ።10Patriarchs and Prophets, p. 176.AHAmh 44.4

    የይስሐቅ ምሣሌነት፦ ወላጆች ለልጆቻቸው የወደፊት ደስታ ያለባቸውን ኃላፊነት ፈጽሞ መዘንጋት የለባቸውም። ይስሐቅ ከአባቱ ሐሳብ ጋር የመስማማቱ ምሥጢር የመታዘዝ ሕ ይወትን እንዲወ ድ በአባቱ የተሰጠው ሥልጠና ውጤት ነው። 11Id., pp. 175, 176.AHAmh 44.5

    ይስሐቅ ዓለም ይባረክበት ዘንድ ያለውን ቃል-ኪዳን ወራሽ እንዲሆን የተመረጠ፣ በእግዚአብሔር እጅግ የከበረ ሰው ነበር። ሆኖም አርባ ዓመት ከሞላው በኋላ ልምድ ያካበተውና እግዚአብሔርን የሚፈራው አገልጋይ ሚስት ይመርጥለት ዘንድ አባቱ የሰጠውን አስተያየት ተቀበለ። ከዚያም ጋብቻ የተገኘው ውጤት ቃሉ እንደሚለው ጣፋጭና ውብ የቤት ውስጥ ደስታ ፍጹም ምሣሌ ሆነ:- “ይስሐቅ ወደ እናቱ ወደ ሳራ ድንኳን አገባት። ርብቃንም ወሰዳት ምሽትም ሆነችለት ወደዳትም። ይስሐቅም ከእናቱ ሞት በኋላ ተጽናና።” 12Id., p. 175.AHAmh 45.1

    ጠቢብ ወላጆች አመዛዛኝና አሳቢ ናቸው፦ እንዲህ ብላችሁ ጠይቁ “ወላጆች ለሴት ወይም ለወንድ ልጆቻቸው ሐሳብና ፍላጎት ሳይጨነቁ የትዳር አጋር ይምረጡላቸው?” ይህን ጥያቄ ለእናንተም አቀርበዋለሁ፤ አንድ ወንድ ልጅ ወይም ሴት ልጅ የሚወዷቸው ወላጆቻቸው ደስታ፣ በምርጫቸው ምክንያት በጣም ሊታወክ እንደሚችል እያወቁ ወላጆቻቸውን ሳያማክሩ የትዳር አጋሮቻቸውን ይምረጡ? ወይስ የአባቱ/ትዋን ምክርና ልመና ቸል ብሎ/ብላ የራሱን/ስዋን ፍላጎት ይከተል/ትከተል? መልሴ በእርግጠኝነት አይደለም ነው፤ ቆመው የሚቀሩ ቢሆን እንኳን። አምስተኛው ትዕዛዝ እንደዚህ አይነት አካሄድ ይከለክላል። “አባትህንና እናትህን አክብር። ዕድሜህ ይረዝም ዘንድ እግዚአብሔር አምላክህ በሚሰጥህ ምድር።” ይህ ትዕዛዝ እግዚአብሔር ለሚታዘዙት በእርግጠኝነት የሚፈጽመውን ቃል-ኪዳን የያዘ ነው። ጠቢብ ወላጆች ለልጆቻቸው ፍላጎት ደንታ ሳይሰጡ የትዳር አጋር አይመርጡላቸውም።13Testimonies for the Church, Vol. 5, p. 108.AHAmh 45.2