Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

የአድቬንቲስት ቤት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First

    ምዕራፍ ስድሳ ስምንት—ማንበብና ተጽዕኖው

    የልጃችሁን አዕምሮ በመልካም መብል መግቡት፦ በቀላሉ የሚማረከውና የሚሰፋው የልጅ አዕምሮ ለዕውቀት ጉጉት አለው። ለልጆቻቸው አዕምሮ መልካም ምግብ ያቀርቡ ዘንድ ወላጆች በቂ እውቀት ያስፈልጋቸዋል። እንደ ሌላው አካል ሁሉ አዕምሮም ኃይሉን የሚያገኘው ከምግብ ነው። በንጹህና በሚያበረታ ሐሳብ አዕምሮ ይሰፋል፤ ከፍ ከፍ ይላል። ምድራዊና አለማዊ በሆነው አስተሳሰብ ግን አዕምሮ ይጠባል፤ ይረክሳልም።AHAmh 299.1

    ወላጆች ሆይ! የልጆቻችሁ አዕምሮ በሚያስከብሩ አስተሳሰቦች የሚመሰጥ ወይም በተንኮል ሀሳብ የተሞላ እንዲሆን የምትወስኑት እናንተው ናችሁ። ንቁ አዕምሮአቸውን ባዶ እንደሆነ ማቆየት አትችሉም፤ ግንባር በመቋጠርም ክፋትን ማባረር አይሆንላችሁም። መጥፎ አስተሳሰብን ማስወገድ የምትችሉት ትክክለኛ መመሪያዎችን በማስረጽ ብቻ ነው። ወላጆች በልጆቻቸው ልቦች የእውነት ዘር ካልዘሩ ጠላት እንክርዳድ ይዘራባቸዋል። መልካም ጠባይን ከሚያበላሸው የክፋት ንግግር የሚጠብቀው ብቸኛው መንገድ መልካምና ቀና ትምህርት ነው። ነፍስ ሊጋፈጠው ካለው የማያባራ ፈተና የሚጠብቀው ደግሞ እውነት ነው።1Counsels to Teachers, Parents and Students, p. 121.AHAmh 299.2

    ወላጆች የልጆቻቸውን የማንበብ ልማድ ሊቆጣጠሩ ይገባቸዋል፦ ብዙ ወጣቶች መጽሐፍ የማንበብ ጉጉት አላቸው። ማግኘት የሚችሉትን ማንኛውንም መጽሐፍ ያነብባሉ። የማንበብ ፍላጎታቸውን ይቆጣጠሩ ዘንድ እንደነዚህ ዓይነት ልጆች ያሏቸውን ወላጆች እለምናለሁ። የፍቅር ታሪክ ያለባቸው ጋዜጦችና መጽሔቶች በጠረጴዛችሁ ላይ እንዲቀመጡ አትፍቀዱ። በዚያ ፈንታ ወደር የሌለውን ለባህርያቸው ግንባታ የሚጠቅማቸውን እግዚአብሔርን ስለመውደድና መፍራት እንዲሁም ስለክርስቶስ ዕውቀት የያዙትን መጻሕፍት አቅርቡላቸው። ዝቅ ላለና ለተዋረደ አስተሳሰብ ቦታ ይጠብባቸው ዘንድ የከበረ እውቀት በአዕምሮአቸው ያከማቹ ዘንድ መልካም የሆነው ሁሉ ነፍስን ይይዝና ጉልበቱንም ይቆጣጠር ዘንድ ልጆቻችሁን አበረታቷቸው። ለአዕምሮ ጥሩ ምግብን ለማያቀርብ ጽሑፍ የማንበብ ፍላጎት እንዲጠፋ መደረግ አለበት።2Id., p. 133.AHAmh 299.3

    የመልካም ነገር ምንጭ ያልሆነ ሁሉ ከቤት እንዲወገድ ወላጆች ያላሰለሰ ጥረት ማድረግ አለባቸው። በዚህ ጉዳይ አንዳንድ ወላጆች ብዙ የሚማሩት ነገር አለ። ልብወለድና የተረት መጽሔቶችን የህሊና ወቀሳ በሌለበት ነፃነት ለሚያነብቡ እንዲህ እላለሁ፡ - የሚያፈራው ፍሬ አንገት የሚያስደፋ ከመሆኑ የተነሳ በኋላ ምርቱን ለመሰብሰብ የማትፈልጉትን ዓይነት ዘር እየዘራችሁ ነው። ከእንደዚህ ዓይነቱ ንባብ የሚገኝ መንፈሳዊ ጥንካሬ የለም። እንዲያውም ለንጹህ የእውነት ቃል ያለውን ፍቅር ያጠፋል። ሰይጣን በትጋት በመልፋት በልብ-ወለድና የታሪክ መጽሔቶች መሳሪያነት የእግዚአብሔርን ቃል ማጥናት የሚገባቸውን አዕምሮዎች እውነትነት በሌለውና በማይረባ አስተሳሰብ በመሙላት ሥራ ላይ ነው። በመሆኑም ፈታኞቹን የሕይወት ቀንበሮች ለመሸከምና በአሸናፊነት ለመወጣት የሚያስፈልጋቸውን ሥነ-ሥርዓት፣ ጉልበትና ጊዜ እልፍ አዕላፋትን እየነጠቃቸው ይገኛል።3Id., pp. 120, 121.AHAmh 299.4

    ልጆች የሚያስፈልጋቸው ተገቢነት ያለው መደሰትና መዝናናትን የሚያመጣ ንባብ እንጂ ግብረ-ገብነታቸውን ዝቅ የሚያደርግ ሰውነታቸውን የሚያዝለፈልፍ አይደለም። የፍቅር ታሪኮችንና የጋዜጦችን ተረታ-ተረቶች እንዲወድዱ ከተለማመዱ ትምህርት ሰጪ ለሆኑ መጻሕፍትና መጣጥፎች ፍላጎት ይጠፋባቸዋል። አብዛኛዎቹ ልጆችና ወጣቶች የሚያነብቡት ነገር አላቸው፤ ካልተመረጠላቸው እራሳቸው ይመርጡታል። በየትኛውም ቦታ አጥፊ የሆነ ንባብ ማግኘት ይችላሉ፤ ሳይዘገዩም ይወዱታል፤ ንጹህና መልካም መጻሕፍት ካቀረቡላቸው ደግሞ ለእንደዚህ ዓይነት ንባብ ፍላጎት ያዳብራሉ።4Review and Herald, Dec. 11, 1879.AHAmh 300.1

    የአዕምሮ መሻት ሥነ-ሥርዓት ሊይዝና ሊገራ ይገባዋል፦ የአዕምሮ ምርጫዎች ከፍተኛ ጥንቃቄ በተሞላበት ሊገሩና ሊሠለጥኑ ይገባቸዋል። አግባብነት ያለው የአስተሳሰብ ልምድ ይመሠረት ዘንድ እየሰፋ ለሚሄደው የልጆች አዕምሮ ገና በለጋ ዕድሜአቸው ወላጆች ቃሉን ሊመግቡት ይገባቸዋል። ትክክለኛ የአጠናን ስልት ለመመሥረት ምንም ጥረት መቆጠብ የለበትም። አዕምሮ መንቀዋለል ከጀመረ መልሳችሁ ወደ ቦታው አምጡት። በገነፈለ ስሜትና በሚያስፈነድቅ የልብ-ወለድ ታሪክ የአዕምሮና የግብረ-ገብነት ምርጫዎች ተጣምመው ሕሊናን በትክክል ለመጠቀም ዝንባሌው ከሌለ ይህንን ልማድ ለማሸነፍ የምንዋጋው ሰልፍ አለ ማለት ነው። ለልብ-ወለድ ንባብ ያለው ፍላጎትና ፍቅር አሁኑኑ መቆም አለበት። አዕምሮ በትክክለኛው መንገድ አርፎ እንዲቀመጥ ጥብቅ ሕጎች መቀመጥና መከበር አለባቸው።5Counsels to Teachers, Parents, and Students, p. 136.AHAmh 300.2

    የልብ-ወለድን ፍላጎት ማበረታታት አቁሙ፦ ልጆቻችን ምን ያንብቡ? ይህ ከባድ ጥያቄ ነው፤ ከባድ መልስም የሚያስፈልገው ነው። ሰንበትን በሚጠብቁ ቤተሰቦች ቤት ውስጥ የሚገኙ ጽሁፎች ጋዜጦችና ተከታታይ የሆኑ ታሪኮች ለልጆችና ለወጣቶች አዕምሮ መልካም አሻራ ትተው የማያልፉ መሆናቸውን ሳይ እጅግ ያሳስበኛል። በእንደዚህ ዓይነት ንባቦች ምክንያት የልብ-ወለድ ፍላጎት ያጎለበቱ አይቻለሁ። እውነቱን የማድመጥና ከእምነታችን እውቀትና ግንዛቤ ጋር እራሳቸውን የማለማመድ ዕድል ነበራቸው፤ ነገር ግን የእውነተኛ ቅድስናና በተግባር የሚገለጽ እግዚአብሔርን መምሰል መካን ሆነው ወደ ጉልምስና አድገዋል።6Id., p. 132.AHAmh 300.3

    ልብ ወለድ የሚያነብቡ ሁሉ የተቀደሰውን ምዕራፍ በመጋረድ መንፈሳዊነትን ለሚያጠፋው ርኩሰት እየተገዙ ናቸው።7The Youth’s Instructor, Oct. 9, 1902.AHAmh 301.1

    ጎጅነት ያላቸው መጻሕፍት መስፋፋት፦ ከሚነበቡ ይልቅ ቢቃጠሉ የተሻለ በሆኑ መጻሕፍት፣ ዓለም ተጥለቅልቃለች። ስሜት ቀስቃሽ ርዕሶች የያዙ የሚታተሙትንና የሚሰራጩትን መጻሕፍት ወጣቶች ፈጽሞ ባያነቧቸው መልካም ነው። በእንደዚህ ኣይነት መጻሕፍት ውስጥ አፍዝዝ አደንግዝ የሆነ ሰይጣናዊ ኃይል አለ….AHAmh 301.2

    ተረት የማንበብ ልምድ ነፍሳትን ለማጥፋት ሰይጣን ከሚጠቀምባቸው መንገዶች አንዱ ነው። ሐሰትና ጤናማ ያልሆነ ጉጉት ይፈጥራል፤ ምናባዊነትን ይቀሰቅሳል። አዕምሮ ለጠቃሚነት ብቁ እንዳይሆን በማድረግ ከመንፈሳዊ እንቅስቃሴው ይከለክለዋል፤ የፀሎትንና የመንፈሳዊ ነገሮችን የፍቅር ጡት ያስጥለዋል።8Counsels to Teachers, Parents, and Students, pp. 133, 134.AHAmh 301.3

    የፍቅር ልብ-ወለድ ታሪኮች እንዲሁም ከንቱና የሚያስፈነድቁ ተረቶች ባልተናነሰ መልኩ ለአንባቢው መርገም ይሆናሉ። ደራሲው የግብረ-ገብነት ትምህርት እንደሚያስተምር ይናገር ይሆናል፤ በመጽሐፉ የኃይማኖት አስተሳሰቦችን ከሌሎቹ ጋር አጠላልፎ ያቀርብ ይሆናል፤ ሆኖም ሁልጊዜ በታች የተደበቀውን ዋጋ-ቢስነትና ከንቱነት ለመሸፈን የሚጠቀምበት ዘዴ ነው።9Ministry of Healing, p. 445.AHAmh 301.4

    ከሐዲ ደራሲያን፦ ያላሠለሰ ጥንቃቄ ልናደርግባቸው የሚገቡን ሌሎች ነገሮች፣ የአደጋ ምንጭ የሆኑትን የከሐዲ ደራሲያንን መጻሕፍት ነው። እነዚህ ሥራዎች የእውነት ጠላት በሆነው አነሳሽነት የተዘጋጁ ናቸው። ነፍሱን አደጋ ላይ ሳይጥል ሊያነብባቸው የሚቻለው ማንም የለም። እውነት ነው የእነዚህ ጽሑፎች ተጠቂ የሆኑ አንዳንዶቹ በመጨረሻ ማገገም ይችሉ ይሆናል፤ ሆኖም ከርኩስ ተጽዕኖአቸው ጋር የሚነካኩ ሁሉ ራሳቸውን በሰይጣን ግዛት ውስጥ ያስቀምጣሉ። እርሱም ያገኘውን ዕድል በዋዛ አያሳልፈውም፤ በእጅጉ ይጠቀምበታል እንጂ። የሚያነቧቸው ሰዎች ፈተናዎቹን ወደራሳቸው ሲጋብዙ ሳለ ክፉውን ለይቶ የማወቅ ጥበብ ወይም የመቋቋም ጉልበት የላቸውም። በሚያቅነዘንዝና መተተኛ በሆነ ኃይል እምነት-የለሽነትና ከሐዲነት ከአዕምሮ ጋር ይጣበቃሉ።10Counsels to Teachers, Parents, and Students, pp. 135, 136.AHAmh 301.5

    አፈ-ታሪኮችና ተረቶች፦ አፈ-ታሪኮች፣ ተረቶችና የፈጠራ ታሪኮች በልጆችና በወጣቶች ትምህርት ውስጥ ሰፊ ቦታ ይዘው ይገኛሉ። የዚህ ዓይነት ባህርይ ያላቸው መጻሕፍት በትምህርት ቤትና በመኖሪያ ቤቶችም ጭምር ይገኛሉ። በውሸት የተሞሉ መጻሕፍት ልጆቻቸው ያነብቡ ዘንድ ክርስቲያን ወላጆች እንዴት ይፈቅዱላቸዋል? እነርሱ ከሚያስተምሯቸው ፈጽሞ ተቃራኒ ስለሆኑት ታሪኮች ትርጉም ሲጠይቋቸው ወላጆች እውነት ያልሆኑ ታሪኮች እንደሆኑ ይነግሯቸዋል። ይህ ግን በመነበባቸው ከሚመጣው ጥፋት አያድናቸውም። በእነዚህ መጻሕፍት የሠፈሩት ሐሳቦች ልጆችን በስህተት ይመሯቸዋል። የተሳሳተ የሕይወት እይታ በማካፈል ገሃድ ላልሆነው ነገር ያላቸው ፍላጎት በውስጣቸው ተወልዶ እንዲያድግ ያደርጋሉ። እውነትን ያጣመመ ይዘት ያላቸው መጻሕፍት በልጆችም ሆነ በወጣቶች እጅ መግባት የለባቸውም። ልጆቻችን ትምህርት በመቅሰም ሂደት ውስጥ ሲያልፉ የኃጢአት ዘሮች የሚሆኑ አስተሳሰቦችን መቀበል የለባቸውም።11Id., pp. 384, 385.AHAmh 301.6

    የአዕምሮ ብርታትና ወኔ እንዴት እንደሚጠፋ፦ የተመዛዘነ አዕምሮ ወይም አስተሳሰብ ያላቸው ብዙዎች አይደሉም። ምክንያቱ ደግሞ መጎልበት የሚያሻውን ደካማ ጎን በመልካም ባህርይ የማነቃቃት፤ መጥፎዎቹን ደግሞ የመጨቆን ሐላፊነት ጠማማነትን በተላበሱ ወላጆች በአሳዛኝ ሁኔታ ቸል ስለሚባል ነው። ልጆቻቸውን በትክክለኛው ልማድና መልካም አስተሳሰብ ማሠልጠን ግዴታቸው እንደሆነ፤ የእያንዳንዱን ልጅ ዝንባሌ በቅርበት ይከታተሉ ዘንድ እጅግ ከባድ በሆነ ኃላፊነት ውስጥ እንዳሉ ይረሳሉ።12Review and Herald, Nov. 12, 1908.AHAmh 302.1

    የግብረ-ገብነትና የአዕምሮ ኃይላትን አጎልብቱ። እነዚህ የከበሩ ኃይላት በልጆች የተረት መጻሕፍት ምንባብ ይደክሙና ይጣመሙ ዘንድ አትፍቀዱ። በንባብ እራሳቸውን መቆጣጠር ባለመቻላቸው የማያመዛዝኑና በከፊል የደነዘዙ ወይም ሽባ የሆኑ፤ ቀድሞ ግን ጠንካራ የነበሩ አዕምሮዎችን አውቃለሁ።13Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 410.AHAmh 302.2

    የሚያጓጉ ጽሑፎች ዕረፍት-የለሽና የህልም እንጀራ የሚበላ ልጅ ይፈጥራሉ፦ የፈጠራና ስሜትን የሚቀሰቅሱ ታሪኮችን የሚያነብቡ፣ እነርሱ ለተግባራዊ የኑሮ ኃላፊነቶች ብቁ አይሆኑም፤ በሕልም ዓለም ውስጥ የሚኖሩ ናቸው። እንደዚህ ዓይነት ታሪኮችን ማንበብ እንዲለማመዱ የተፈቀደላቸውን ልጆች ተመልክቻለሁ። በቤትም ሆነ በውጭ ዕረፍት የሌላቸው ምናባዊና በጣም ከተለመደና ተራ ከሆነ ነገር በቀር ስለሌላ ጉዳይ ማውራት የማይችሉ ነበሩ። ኃይማኖታዊ አስተሳሰብና ንግግር ለአዕምሮአቸው ባይተዋር ነበር። በስሜታዊ ታሪኮች ፍላጎት ተገንብቶ አዕምሮን የሚጣፍጠው ነገር ተበላሽቶ ስላለ ይህንን ያልተመጣጠነ ምግብ ካልበላ በስተቀር ሕሊና እርካታ አያገኝም። በእንደዚህ ዓይነቱ ምንባብ ለሚረኩ ሁሉ የሰከሩ ናቸው ከማለት ውጪ ሌላ ስም ላገኝላቸው አልችልም። ያልተቆጠበ መብልና መጠጥ የመውሰድ ልማድ በሰውነት ላይ የሚያመጣውን ችግር ያህል ከቁጥጥር ውጭ የሆነ የማንበብ ልማድም በአንጎል ላይ ተመሳሳይ ጉዳት ያመጣል።14Counsels to Teachers, Parents, and Students, pp. 134,135.AHAmh 302.3

    አንዳንዶች እውነትን ከመቀበላቸው አስቀድሞ ልብ-ወለድ የማንበብ ልምድ መሥርተዋል፤ ወደ ቤተ-ክርስቲያን ሲቀላቀሉ ይህንን ልምድ ለመተው ይጥራሉ፤ ለእነዚህ ሰዎች ከተዋቸው ንባቦች ጋር የሚመሳሰሉ ጽሑፎችን ማቅረብ ለሰከሩ ሰዎች ተጨማሪ አስካሪ መጠጦች እንደመስጠት ነው። በተደጋጋሚ በፊታቸው ለሚጋረጠው ፈተና እጅ በመስጠት ሳይቆዩ ጠጣር ለሆኑ ንባቦች ጣዕም ይጠፋባቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ የማንበብ ፍላጎት አይኖራቸውም፤ የግብረ-ገብነት ኃይላቸው ይልፈሰፈሳል። የኃጢአት ቀፋፊነት እየቀነሰባቸው ይሄዳል፤ የእምነት-አልባነት መጨመር እየተንፀባረቀ ለሕይወት ተግባራዊ ኃላፊነቶች ፍላጎት እየጠፋ ይሄዳል። አዕምሮ እየተበላሸ ሲሄድ የማነሣሳት ባህርይ ያለውን ማንኛውንም መጽሐፍ ለማንበብ ዝግጁ ይሆናል። በዚህም ሁኔታ ነፍስ ሙሉ በሙሉ በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ትሆን ዘንድ በሩ ወለል ብሎ ይከፈታል።15Testimonies for the Church, Vol. 7, p. 203.AHAmh 302.4

    ችኩልና ጥልቅነት የሌለው አነባበብ የማስተዋል ኃይልን ይቀንሳል፦ ከማተሚያ ቤቶች ያለማቋረጥ በሚወጣው የህትመት ማዕበል ትንሹም ትልቁም ችኩልና ማስተዋል የሌለው አነባበብ ተለማምዷል። በዚህ መሀል ጭንቅላት ብርቱና የተቀናጀ ኃይሉን ያጣል። እንደ ግብጽ እንቁራሪቶች ምድሩን ሁሉ የሚሞሉት በየወቅቱ የሚታተሙ መጽሔቶችና መጻሕፍት ተራ ከንቱና የሚያደክሙ ብቻ ሳይሆኑ የቆሸሹና ካለን ደረጃ ዝቅ የሚያደርጉን ናቸው። ጉዳታቸው አዕምሮን በማስከርና በማጥፋት አያበቃም፤ ነፍስን እስከ ማበላሸት ብሎም እስከ ማውደም ይዘልቃል።16Education, p. 189, 190.AHAmh 303.1

    “የቤተ-ክርስቲያናችንን ጽሑፎች የመግዛት አቅም የለኝም”፦ ወንድሞች እንደሆኑ የሚናገሩ ከዓለማዊ መጽሐፎች አንድ ወይም ሁለት ሲወስዱ ሳለ Review, Signs, Instructor ወይም Good Healthን ግን ንክች የማያደርጉ አሉ። በየጊዜው የሚወጡትን እውነት የተሸከሙትን ጽሑፎቻችንንና ሕትመቶቻችንን መግዛት እንደማይችሉ ቢናገሩም ልጆቻቸው እጅግ የሚወዷቸውን የፈጠራ ወሬዎችና የፍቅር ታሪኮች የያዙትን መጣጥፎች የመግዛት አቅም ግን አላቸው….AHAmh 303.2

    ልጆቻቸው ንጹህ አስተሳሰብ ያዳብሩ ዘንድ በጋዜጦች ውስጥ የሚገኙ በእጅ የተሳሉ የፍቅር ገመምተኛ ሥዕሎችን ልክ ቁምጥናን እንደሚሸሹ ይርቋቸው ዘንድ ወላጆች ሊያስተምሯቸውና ሊጠብቋቸው ይገባል። ልጆቻችሁ የከበረ ነገር የማንበብ ልምድ ያዳብሩ ዘንድ ጠረጴዛዎቻችሁና ቤተ-መጽሐፍቶቻችሁ የግብረ-ገብነትና የኃይማኖት ጉዳዮችን በያዙ ሕትመቶች ይሞሉ።17Review and Herald, Dec. 11, 1879.AHAmh 303.3

    ስለማንበብ ጥቅም ለወጣቶች የተሰጠ መልእክት፦ አግባብነት በሌለው ምንባብ ምክንያት በወጣቶች ላይ የተጋረጠውን አደጋ ስመለከት፣ ስለዚህ ታላቅ ርኩሰት የተሰጠኝን ተጨማሪ ማስጠንቀቂያ ከመስጠት መታቀብ አልቻልኩም። ሊቃወሙት የሚገባ ባህርይ ያዘሉ ጉዳዮች ላይ መሥራት፣ ሠራተኞቹ ላይ ምን ያህል ጉዳት እንደሚያደርስ የታወቀው በጣም ጥቂቱ ነው። ትኩረታቸው ይያዝና በተጠመዱበት ጉዳይ ፍላጎታቸው ይነሳሳል። ዓረፍተ-ነገሮች በአዕምሮአቸው ይታተማሉ፤ ኃሳቦችም በአስተያየት መልክ ይቀርባሉ። ሳያውቀውና ሳያስተውለው አንባቢው በጸሐፊው ተጽዕኖ ሥር ይወድቃል። አዕምሮና ባህርይ የክፋት አሻራ ይወስዳሉ። እምነት የሌላቸውና እራሳቸውን የመቆጣጠር ኃይል በእጅጉ ያነሳቸው አሉ፤ እነዚህ ሥነ-ጽሑፎች የሚጠቁሙትን አማራጭና ያሳደሩትን የአስተሳሰብ ተጽዕኖ ለማስወገድ አስቸጋሪ ይሆንባቸዋል።18Testimonies for the Church, Vol. 7, p. 203AHAmh 303.4

    ኦ! ስሜት ቀስቃሽ ጽሑፎች በአዕምሮ ላይ ያላቸውን ተጽዕኖ ወጣቶች ማየት ቢችሉ ኖሮ! ከእንደዚህ ዓይነት ንባብ በኋላ የእግዚአብሔርን መጽሐፍ ከፍታችሁ የሕይወትን ቃል በፍላጎት ታነቡታላችሁ? የእግዚአብሔር መጽሐፍ የማይስብ ሆኖ አላገኛችሁትም? የሚያፈዝዘው የፍቅር ታሪክ የአዕምሮን ጤናማ ቃና ያጠፋውና የዘለዓለም ጉዳይን ባዘሉ በጠቃሚና በከበሩ እውነቶች ላይ ማነጣጠር እንዳትችሉ ያደርጋል። ለዚህ የዘቀጠ ዓላማ ጊዜያችሁን ስለሰዋችሁ በወላጆቻችሁ ላይ ኃጢአት ትሠራላችሁ፤ ለእርሱ የተገባውን ጊዜም በከንቱ ስላጠፋችሁ እግዚአብሔርን ትበድላላችሁ።19Id, Vol. 2, p. 236.AHAmh 304.1

    ልጆች ሆይ! ለእናንተ መልእክት አለኝ። የወደፊት ዕጣ ፈንታችሁን የምትወስኑት አሁን ነው፤ እየገነባችሁት ያላችሁት ባህርይ ከእግዚአብሔር ገነት የሚያስቀራችሁ ዓይነት ነው። ለእግዚአብሔር ፍቅርና ለቃሉ ክብር የሌላቸውን የተረት መጻሕፍትን የማንበብ አባዜ የተጠናወታቸውን ልጆች ያሉበትን ቤተሰብ መመልከት ለዓለም መድኃኒት ለክርስቶስ እንዴት አሳዛኝ ክስተት ነው! በእንደዚህ ዓይነት መንገድ የሚጠፋው ጊዜ በቤተሰብ ሥራ ውስጥ ባላችሁ ተሳትፎ ውጤታማ እንዳትሆኑ ያደርጋችኋል። የቤተሰብ እራስነት እርከንን እንዳትቆናጠጡ ከማድረጉም በላይ ካልተገታ በስተቀር ወደ ሰይጣን ወጥመድ የበለጠ እያስጠጋችሁ ይሄዳል። አንዳንድ የምታነቧቸው መጻሕፍት ግሩም መርሆዎችን የያዙ ናቸው፤ የምታነቧቸው ግን ለታሪካቸው ብቻ ነው። ከምታነቧቸው መጻሕፍት ባህርያችሁን በመልካም ለመቅረጽ የሚረዷችሁን ለቅማችሁ ብታወጡ የተወሰነ መልካም ነገር በሆነላችሁ ነበር። ነገር ግን መጽሐፎቻችሁን አንስታችሁ ገጽ በገጽ ስታነቧቸው የማንበባችሁ ዓላማ ምንድን ነው? ጠቃሚ የሆነ እውቀት ለማግኘት እየጣርሁ ነው ብላችሁ ጠይቃችሁ ታውቃላችሁ? የመሠረት ድንጋይ መሆን በማይችሉት፣ በእንጨት፣ በሳርና በገለባ ትክክለኛውን ባህርይ መገንባት አትችሉም።20Letter 32, 1896.AHAmh 304.2

    የመጽሐፍ ቅዱስ እውነትን በአዕምሮ ውስጥ ዝሩ፦ ጠፍ በተተወ መሬትና ባልሠለጠነ አዕምሮ የሚገርም ተመሳሳይነት አለ። በልጆችና በወጣቶች አእምሮ ጠላት እንክርዳድ ይዘራል፤ ወላጆች ጥብቅ ቁጥጥር ካላደረጉ አድገው የጥፋት ፍሬን ያፈራሉ። ያላሰለሰ ጥንቃቄ በማድረግ የአዕምሮን ማሳ በማረስ የከበረው የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ሊዘራበት አስፈላጊ ነው። ልጆች ርካሽና ስሜትን የሚቀሰቅሱ ወሬዎችን ማንበብ እንዲጠሉ በምትኩም አዕምሮን ወደ መጽሐፍ ቅዱስ ታሪክና ሐሳብ ወደሚመሩት ወደ ትርጉም ሰጭ መጻሕፍት እንዲዞሩ መማር አለባቸው። በተቀደሰው መጽሐፍ ላይ ብርሃን የሚያበራ ይነበብም ዘንድ የሚያስቸኩለው ፍላጎት ጠቃሚ እንጂ አደገኛ አይደለም።21Counsels to Teachers, Parents, and Students, pp. 136, 137AHAmh 304.3

    የእግዚአብሔርን ቃል በጥሞና ማንበብ ደስታ የማይሰጠው ከሆነ ወጣቱ ጤናማ የአዕምሮ ቅኝት ሊይዝ ፈጽሞ የማይቻለው ነው። ይህ መጽሐፍ [መጽሐፍ ቅዱስ] እጅግ የሚማርኩ ታሪኮችን የያዘ በክርስቶስ በኩል የመዳንን መንገድ የሚያመላክት ለከፍተኛውና ለተሻለው ሕይወት መሪ የሚሆን ነው።22Testimonies for the Church, Vol. 2, pp. 410, 411.AHAmh 305.1