Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

የአድቬንቲስት ቤት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ ሠላሳ ሰባት—መሆን የማይገባችሁ የባል ዓይነት

    ሚስት እጥፍ ሸክም እንድትሸከም የሚጠብቅ ባል፦ በብዙ ቤተሰቦች በተለያየ የዕድሜ ክልል ያሉ የእናታቸው ትኩረትና ብልህ መመሪያ ብቻ ሳይሆን፣ የጥብቅ ሆኖም የአፍቃሪ አባታቸው ተጽዕኖ የሚያስፈልጋቸው ብዙ ናቸው። እነዚህ ነገሮች ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆኑ የሚገነዘቡ አባቶች ግን ብዙ አይደሉም። የእራሳቸውን ኃላፊነት ቸል ብለው ከባድ ሸክም በሚስታቸው ላይ መጫናቸው ሳያንስ እንዳሻቸው እርስዋኑ ለመኮነንና ለማውገዝ የሚገድባቸው ነገር እንደሌለ ይሰማቸዋል። በዚህ ከባድ ኃላፊነትና ተግሳፅ ሥር ምስኪንዋ ሚስትና እናት፣ በቅንነት ከሁኔታዎች ከባድነት አንፃር የተቻላትን ሁሉ በብቃት ለማድረግ ብትጥርም፣ ሁልጊዜ የጥፋተኝነትና የፀፀት ስሜት ይሰማታል። ሆኖም እነዚህ አድካሚ ጥረቶችዋ ሊመሠገኑና ሊሞገሱ፤ ልብዋም ደስ ሊለው ሲገባ በሃዘንና በውግዘት ሥር እንድትራመድ ትገደዳለች። ምክንያቱ ደግሞ ባል የራሱን ኃላፊነት ቸል ብሎ ሚስቱ በምን ሁኔታ ውስጥ እንዳለች ሳይረዳት የሁለቱንም ግዴታዎች እርሱ እንደሚፈልገው እንድታሟላ ስለሚፈልግ ነው። 1Signs of the Times, Dec. 6, 1877.AHAmh 155.1

    ሚስቶቻቸው ቀኑን ሙሉ በማያቋርጥ የቤት ውስጥ ሥራ ሲባክኑ መዋላቸውንና በምን ያህል ጭንቀትና ግራ መጋባት ውስጥ እንደሚያልፉ ብዙ ወንዶች አይረዱም። ብዙ ጊዜ ለቤተሰቡ ፈገግታ ሳይሆን የተቋጠረ ፊት ይዘው ወደ ቤት ይገባሉ። በሥራ የዛለች ሚስት የቤት ጽዳት ነርስ፣ ምግብ አብሳይና ሰራተኛ ሁሉንም ሆና ሳለ ምግብ በሰዓቱ ካልደረሰ የኩነኔ ሠላምታ ይሰጣታል። ለቤተሰቡ የምታዘጋጀው ምግብ ይፋጠን ዘንድ አስቸጋሪውን ልጅ ከዛለው ከሚስቱ ክንድ ለመውሰድ አቃቂር አውጪው ባል ይስማማ ይሆናል። ሆኖም ዕረፍት- የለሹ ሕፃን በአባቱ ክንድ ሲንከላወስ ማባበልና ዝም ማስባል የእርሱ ኃላፊነት ሆኖ አይሰማውም። እናቱ ለምን ያህል ሰዓት ከህፃኑ ጋር በመሆን ክልፍቱነቱን(እረፍት-ቢስነቱን) እንደቻለች ለማጤን ጊዜ ሳይሰጥ ይጣራል፡- “ይኸው እናት ልጅሽን ውሰጂ!” ይላል። የእርስዋ ልጅ ብቻ እንደሆነ ሁሉ! የእርሱስ አይደለምን? ልጆቹን የማሳደግ ሸክም በትዕግስት ሊሸከም ግዴታ የለበትምን? 2Signs of the Times, Dec. 6, 1877.AHAmh 155.2

    ፈላጭ ቆራጭና የበላይነት ለሚያሳይ ወንድ የተሰጡ የምክር ቃላት፦ባልና አባት ስለሆንህ ፍጹም ሥልጣን እንደተሰጠህ የሚሰማህን አጉል ስሜት ብትተወው ሕይወትህ የበለጠ ደስተኛ ይሆን ነበር። ተግባርህ የሚያሳየው ደረጃህን በስህተት እንደተረጎምኸው ነው፤ የስምህ ትርጉም የቤት ማገር ማለት ነውና። ብስጩነትህና ፈላጭ ቆራጭነትህ የማመዛዘን ጉድለት እንዳለብህ ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፤ በመሆኑም አንዳንድ ጊዜ ለማስተካከል ጥረት ብታደርግም እንኳ ለሚስትህና ለልጆችህ ያልተዛነፈ ፍርድ መስጠት እንደምትችል ማሳየት ይሳንሃል። አንድ ጊዜ አቋም ከወሰድህ በኋላ ሐሳብህን ለመቀየር በአብዛኛው ፈቃደኛ አይደለህም። ትክክለኛውን መንገድ እየተከተልህ እንደሆነ መመርመር ሲገባህ በተደጋጋሚ እቅድህን ለማስፈፀም ቆርጠህ ትነሣለህ። ጨምሮ ጨማምሮ የሚያስፈልግህ ፍቅርና ታጋሽነት ነውና በቃልና በተግባር ውሳኔህን ለማስፈጸም ያለህን ግትርነት ቀንሰው። አሁን የምትከተለው አካሄድ የቤት ማገር በመሆን ፈንታ ሌሎችን ለመጨቆንና ለማስጨነቅ የተቀመጥህ መቆንጠጫ መሳሪያ አድርጎሃል…. የራስህን ሐሳብ ለማስፈጸም ሌሎችን በምታስገድድበት አጋጣሚ ሁሉ ውሳኔህን ብትቀይር እራስህ ከምትጎዳው የባሰ ይህንን የማን-አለብኝ ግትርነትህ ስለቀጠልክበት በሌሎች ላይ የከፋ ጉዳት ታደርሳለህ። የያዝሃቸው ሐሳቦች በራሳቸው እውነት ሊሆኑ ይችላሉ፤ ከብዙ አቅጣጫ ሲታዩ ግን ትክክል አይደሉም። ከአደረጃጀትህ ልዩነት የተነሳ ሐሳቦችህንም በስህተት ተጠቅመህባቸዋል፤ በጠንካራና አመዛዛኝነት በሌለው ሁኔታ እንዲተገበሩ ጥረሃል። 3Letter 19a, 1891.AHAmh 155.3

    ቤተሰቦችህን በማስተዳደር ረገድ ለየት ያለ እይታ ያለህ ነህ። ለሌሎች ፍላጎት ነፃነት የማይሰጥ ግላዊና ፈላጭ ቆራጭ የሆነ ኃይል ትጠቀማለህ። የቤት አስተዳዳሪነትህን በራስህ ፍፁም እንደሆነ አድርገህ፤ ማሽን በሠራተኞቹ እጅ እንደሚሸከረከር ያንተ ጭንቅላት ብቻውን የቤተሰቡን አባላት ለማሽከርከር በቂ ነው ብለህ ታስባለህ። በሥልጣንህ የምትፈልገው ሁሉ እንዲፈጸምልህ ታስገድዳለህ። ይህ ሰማይን የሚያስከፋ፣ ሩኅሩኅ መላእክትን የሚያሳዝን ነው። አንተ ብቻህን ቤተሰቡን ማስተዳደር የምትችል መሆኑን ለቤተሰቡ በምትሰጠው መልስህ አሳይተሃል። ባለቤትህ አስተያየትህን መቃወሟ ወይም ውሳኔህን ጥያቄ ውስጥ ማስገባትዋ አስከፍቶሃል። 4Testimonies for the Church, Vol. 2, p. 253.AHAmh 156.1

    ብስጩና ነዝናዛ ባሎች፦ ባሎች ሆይ ለሚስቶቻችሁ መንፈሳዊ ሕይወት እድል ስጡ.... በአብዛኛው [የብስጭት ፀባይ] በባሎች ዘንድ ልክ ጎረምሳ እስኪመስሉ ድረስ ጎልቶ ይታያል። ይህን የልጅነት ሕይወታቸው አካል የሆነውን ባህርይ አልተውትም ማለት ነው። ይህንን ስሜት በማበረታታታቸው ምክንያት ሕይወታቸው ምሬት በተሞላበት ንዝንዝ የታቆረ፣ የሰለለና የደኮረ ይሆናል። ይህም የእነርሱን ሕይወት ብቻ ሳይሆን የሌሎቹንም ይጨምራል። እጁ በሌሎች ላይ የነበረች የሌሎቹ እጅ ደግሞ በእርሱ ላይ የነበረችውን የእስማኤልን መንፈስ የተሸከሙ ናቸው። 5Letter 107, 1898.AHAmh 156.2

    የሚያስመርሩና ነዝናዛ ባሎች፦ ወንድም ቢ(B) ወደ ቤቱ ደስታን የሚያመጣ ዓይነት ጠባይ የለውም። ይህ ሥራ ሊጀመርበት የሚገባ ጥሩ ቦታ ነው። ከብርሃን ጮራ ይልቅ ጭጋግ ይመስላል። እጅግ ራስ-ወዳድ ከመሆኑ የተነሣ ለቤተሰቡ አባላት በተለይም ከሁሉም በላይ ፍቅርና አክብሮት ለሚገባት ባለቤቱ አድናቆት መቸር አይፈልግም። አኩራፊ ጨቋኝና አምባገነን ነው። መንፈሱን በማለዘብ፣ ጥፋቱን በመቀበልና ለሠራው ስህተት ይቅርታ በመጠየቅ ሊፈውስ የማይሞክረው ንግግሩ የሚያደማና የሚያቆስል ነው….AHAmh 156.3

    ወንድም ቢ መለስለስ ይገባዋል፤ ርኅራኄንና ንጽህናን ሊያጎለብት ይገባዋል። በሁሉም ነገር እኩል ለሆነችው ሚስቱ የዋህና ደግ ሊሆንላት ይገባል። በልብዋ ጥላ የሚጥል አንድም ቃል መናገር የለበትም። የተሃድሶን ሥራ በቤት መጀመር አለበት። ፍቅርን በማጎልበት ከርዳዳ፣ ጨካኝ፣ ሐዘኔታ የሌለውንና ገብጋባ ባህርይውን ለማሸነፍ ይሞክር። 6Testimonies for the Church, Vol. 4, pp. 36, 37.AHAmh 157.1

    አኩራፊ፣ ራስ-ወዳድና ጨቋኝ የሆነ ባልና አባት ለራሱ ደስታ የሌለው መሆኑ ብቻ ሳይሆን በነዋሪዎቹ ሁሉ ላይም ትካዜን ይጥላል። በራሱ መልካም ባልሆነ ጠባዩ ምክንያት የታወኩትን ልጆቹን፣ የታመመችና ተስፋ የቆረጠች ሚስቱን በማየት የዘራውን ያጭዳል። 7Ministry of Healing, pp. 374, 375.AHAmh 157.2

    ለራሱ ብቻ የሚያስብና የማይታገስ ባል፦ ከባለቤትህና ከልጆችህ ከመጠን ያለፈ ትጠብቃለህ። ተግሳፅህ መረን የለቀቀ ነው። ፈገግተኛና ደስተኛ የሆነ ጠባይን ለራስህ ብታሳይ በቸርነትና በገራምነት ብታናግራቸው ከደመና፣ ከሐዘንና ከትካዜ ይልቅ እንደ ፀሐይ ጮራ የሚያንፀባርቅ ደስታ ወደ መኖሪያህ ማምጣት ትችላለህ። ስለራስህ ሐሳብ ብዙ ትብከነከናለህ፤ የተራራቁ ሐሳቦችን በማራመድ የሚስትህ አስተያያት ሊኖረው የሚገባውን ክብደት ለመስጠት ፈቃደኛ አይደለህም። ሚስትህን እንድታከብራት እራስህን አላበረታታኸውም፤ ሚስትህ የምታሳልፈውንም ውሳኔ ልጆችህ እንዲያከብሩት አላደረግሃቸውም። የማስተዳደሩን ስልጣን በእጅህ ጨምድደህ ይዘህ፣ በራስህ ቁጥጥር ሥር ብቻ በማድረግ እርስዋን አቻህ አላስመሰልካትም። አፍቃሪና ሐዘኔታ ያለው ጠባይ የለህም። አሸናፊ መሆንና የእግዚአብሔር በረከት በቤተሰብህ ላይ እንዲሆን ካማረህ እነዚህን ባህርያት [ፍቅርና ርኅራኄን] ማጎልበት ያስፈልግሃል። 8Testimonies for the Church, Vol. 4, p. 255.AHAmh 157.3

    ለክርስቲያናዊ ደግነት ቁብ ለማይሰጥ ወንድ፦ ደግ፣ ጨዋና ሩኅሩኅ መሆንን እንደ ሽንፈት በመቁጠር በልስላሴ በደግነትና በፍቅር ሚስትህን ማናገር ክብርህን ዝቅ የሚያደርገው መስሎ ተሰምቶሃል። እውነተኛ ወንድነትና ክብር ምን ማለት እንደሆነ እዚህ ላይ ስተኸዋል። የቸርነት ድርጊቶችን ሳትፈጽም የመተው ዐመልህ ያለብህን የባህርይ ድክመትና ጉድለት የሚያሳይ ነው። አንተ ደካማነት ነው ብለህ የናቅኸው በእያንዳንዱ ክርስቲያን ሊንፀባረቅ የሚገባው ክርስቲያናዊ ደግነት ነው ይላል፣ እግዚአብሔር፤ ክርስቶስ ያሳየው ባህርይ ይህ ነበርና። 9Id., p. 256.AHAmh 157.4

    ባሎች ፍቅርንና መውደድን መሻት የተገባቸው ይሁኑ፦ ባል ጨካኝ፣ በቃኝ የማይል፣ አድራጎትዋን የሚኮንንና የሚተች ከሆነ ፍቅርና አክብሮትዋን ጠብቆ ሊያቆይ አይችልም፤ ትዳርም የሚያስጠላ ይሆንባታል። ራሱን ተወዳጅ ለማድረግ ስለማይጥር ባልዋን አትወደውም። ባሎች ጥንቁቆች፣ ትኩረት ሰጪዎች፣ የማይዋዥቁ፣ ታማኞችና ሩህሩሆች መሆን ይጠበቅባቸዋል። ርኅራኄና ፍቅር ሊያንፀባርቁ ይገባቸዋል። ሁሉም ክርስቲያን ሊኖረው እንደሚገባ ባልየው የተከበረ ባህርይ፣ የልብ ንጽህናና ከፍ ከፍ ያለ አዕምሮ ያለው ከሆነ፣ ይህ ምግባሩ በትዳሩ ውስጥ የሚገለጽ ይሆናል…. ሚስቱ ብርቱና ጤናማ እንድትሆን ይጥራል። በቤት ውስጥ ሠላም የሰፈነበት ሁኔታ ለመፍጠርና የሚያጽናኑ ቃላትን ለመናገር ይተጋል። 10Manuscript 17, 1891.AHAmh 158.1

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents