Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents

የአድቬንቲስት ቤት

 - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First

    ክፍል ፫—የሕይወት አጋርን መምረጥ

    ምዕራፍ ስድስት—ታላቁ ውሳኔ

    ደስተኛ ወይስ ሐዘን የሞላበት ጋብቻ፦ ስለ ትዳር የሚያስቡ ሁሉ ከጋብቻ በኋላ ስላላቸው ሕይወት አሰቃቂና ሐዘን የሞላበት ዕይታ እንዳይኖራቸው ከፈለጉ አሁን የምርና እውነተኛ ጉዳይ ያድርጉት። ይህ እርምጃ ጥበብ በጎደለው አኳኋን ሲተገበር የወጣት ወንዶችንና ሴቶችን ጠቀሜታ ከሚያጠፉት አንዱና ዋናው መንገድ ይሆናል። ሕይወት ሸክምና እርግማን ይሆናል። የአንዲትን ሴት ደስታና ጠቃሚነት በማበላሸት፣ ሕይወትዋንም ልብን የሚያሳምም ሸክም በማድረግ ረገድ እንደ ባልዋ ውጤታማ የሚሆን ሌላ ማንም ሰው የለም። የአንድን ወንድ ምኞትና ተስፋ በማቀዝቀዝ፣ ኃይሉን ሽባ በማድረግ፣ የወደፊት ተጽዕኖውንና ተስፋውን በማፈራረስ እንደ እራሱ ሚስት አንድ መቶኛ ያህል እንኳ የሚሳካለት ሰው የለም። የብዙ ወንዶችና ሴቶች ስኬት ወይም ውድቀት በዚህ ምድር እንዲሁም የወደፊቱ ሕይወት ተስፋቸው የሚወሰነው ከጋብቻ ሰዓት ጀምሮ ነው።1Review and Herald, Feb. 2, 1886.AHAmh 22.1

    ወጣቶች የተጋረጠባቸውን አደጋ እንዲያዩና እንዲያውቁ ማድረግ ብችል እንዴት በወደድሁ ነበር፤ በተለይ ደስታ-ቢስ የሆነ ትዳርን የመመሥረት አደጋ።2Testimonies for the Church, Vol. 4, p. 622.AHAmh 22.2

    ጋብቻ በዚህ ምድርና በሚመጣውም ዓለም ሕይወታችን ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድርና ሊያቃውስም የሚችል ነው። አንድ ልባዊ ክርስቲያን እግዚአብሔር አካሄዱን እንዳጸደቀለት ሳያውቅ የራሱን እቅድ በዚህ አቅጣጫ አይተገብርም። እራሱ መምረጥ ሳይሆን እግዚአብሔር ሊመርጥለት እንደሚገባ ይሰማዋል። እራሳችንን ልናስደስት አይገባንም፤ ክርስቶስ እራሱን ደስ አላሰኘምና። ማንም ሰው የማያፈቅረውን ያግባ እያልሁ እንዳልሆነ ትረዱኛላችሁ፤ ይህ ኃጢአት ይሆናል። ነገር ግን ስሜታዊ ተፈጥሮና ምኞት ወደ ጥፋት እንዲመሩን ልንፈቅድላቸው አይገባም። እግዚአብሔር ሙሉ ልብንና ብልጫ ያለው ፍቅርን ይፈልጋል።3Review and Herald, Sept. 25, 1888.AHAmh 22.3

    ጥድፊያን በዝግታ አድርጉ (በዕርጋታ ፍጠኑ)፦ ስለ ጋብቻ ግንኙነት ትክክለኛ መረዳት ያላቸው በጣም ጥቂቶች ናቸው። ትዳርን ብዙዎች ፍፁም ተድላና ደስታ የሚገኝበት አድርገው የሚያስቡ ይመስላል። በጋብቻ የቃል-ኪዳን ሰንሰለት የተጠፈሩትን፤ ሊበጥሱት የማይችሉትን ወይም ሊቆርጡት ድፍረት ያጡትን፤ የወንዶችና የሴቶች የልብ ውጋት የሆነውን ትዳር አንድ አራተኛውን ቢያውቁት ኖሮ ግን በዚህ አባባሌ አይገረሙም ነበር። ትዳር ለአብዛኛው ሰው የሚያበሳጭ ቀንበር ነው። በትዳር የተቆራኙ ነገር ግን ያልገጠሙ(ያልተጣጣሙ) በሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው። በትዳር ካባ ሥር ተደብቆ ያለ እንጉርጉሮ፣ ርጉምነትና ግፍ የሰማይ መጻሕፍትን አጨናንቆ ይገኛል። ለዚህ ነው ለጋብቻ የደረሱትን ወጣቶች አጋራችሁን የመምረጥ ጥድፊያን በዝግታ አድርጉት የምላቸው። የትዳር ጎዳና ውብና ደስታ የሞላበት ይመስላል፤ ነገር ግን በሺዎች የሚቆጠሩ ቅር እንደተሰኙ እናንተስ የማትከፉበት ምን ምክንያት አለ?4Review and Herald, Feb. 2, 1886.AHAmh 22.4

    ለማግባት የሚያስቡ ሁሉ የሚመሠርቱት ትዳር መልኩና ተጽዕኖው ምን እንደሚመስል መመርመር አለባቸው። ባለትዳሮች ወላጆች ወደ መሆን ሲመጡ የከበረ አደራ የሚጣልባቸው ናቸው። በዚህ ዓለም የልጆቻቸው ህልውና፤ በሚመጣው ዓለም ደግሞ ደስታቸው የሚወሰንበት ነው። በአብላጫው ወላጆች ሕፃናት የሚቀበሉትን የአካላዊና ግብረ-ገባዊ ማህተም የሚወስኑ ናቸው። የማህበረሰቡ ሁኔታም በቤት ውስጥ ባለው ባህርይ ይወሰናል፤ የእያንዳንዱ ቤተሰብ ተጽዕኖ ክብደት የማህበረሰቡን የመልካም ወይም የክፋት ሚዛን ከፍ ወይም ዝቅ እንዲል ያደርገዋል።5Ministry of Healing, p. 357.AHAmh 23.1

    በምርጫ ጊዜ ወሳኝ የሆኑ መስፈርቶች፦ ጓደኝነት በመመሥረትና አጋርን በመምረጥ ረገድ በክርስቲያን ወጣቶች ዘንድ ትልቅ ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል። ተጠንቀቁ! አሁን ንጹህ ወርቅ ነው ብላችሁ ያሰባችሁት ተራ ብረት ሆኖ እንዳታገኙት። ዓለማዊ ቁርኝቶች እግዚአብሔርን ከማገልገል የሚገድቡን እንቅፋቶች ይሆናሉ። ደስታ በሌለው የሥራ ወይም የጋብቻ ህብረት ምክንያት ብዙ ነፍሳት ፈጽሞ ከፍ ከፍ ሊያደርጉ ወይም ስብዕናን ሊገነቡ ከማይችሉ ሰዎች ጋር አብረው ጠፍተዋል።6Fundamentals of Christian Education, p. 500.AHAmh 23.2

    እያንዳንዱን ስሜት መዝኑ፤ የሕይወት ዕጣችሁን ልታቆራኙት የምታስቡትን ሰው እያንዳንዱን የባህርይውን እድገት ተመልከቱ። ልትወስዱት ያለው እርምጃ በሕይወታችሁ በጣም አስፈላጊ ከሚባሉት አንዱ ነውና በችኮላ አታድርጉት። ብታፈቅሩም እውር ፍቅር አይሁን። AHAmh 23.3

    የጋብቻ ሕይወታችሁ ደስተኛ ወይስ ስምምነት የሌለውና የተንኮታኮተ የሚሆን እንደሆነ ማየት ትችሉ ዘንድ በጥንቃቄ መርምሩት። እንዲህ ዓይነት ጥያቄዎች ይነሱይህ ጥምረት ወደ ሰማይ ይመራኛል? ለእግዚአብሔር ያለኝን ፍቅር ይጨምርልኛል? ይህ ሕይወት የጠቃሚነቴን አድማስ ያሰፋልኛል? የእነዚህ ጥያቄዎች መልሶች አወንታዊ ከሆኑ ከፈሪሃ-እግዚአብሔር ጋር በጥንቃቄ ወደ ፊት ተራመዱ።7Id., pp. 104, 105.AHAmh 23.4

    ብዙ ወንዶችና ሴቶች ወደ ጋብቻ ግንኙነት ለመግባት መጠየቅና መመለስ ያለበት ብቸኛ ጥያቄ ሁለቱ ይፋቀራሉ ወይ የሚለው እንደሆነ ያምናሉ። ነገር ግን ከዚያ በተጨማሪ ኃላፊነት እንደሚወድቅባቸው ማስተዋል አለባቸው። ከአብራካቸው የሚወጡት በአካል ጤናማ በአዕምሮና በስነ-ምግባር ጠንካራ መሆን እንደሚችሉ ይመርምሩ። ነገር ግን በቀላሉ ገፍትረው በማይጥሉት ከፍተኛ ተነሳሽነትና የከበረ አስተሳሰብ የሚንቀሳቀሱ በጣት የሚቆጠሩ ናቸው። የህብረተሰብ ተጠያቂነት እንዳለባቸውና የቤተሰባቸው የተጽዕኖ ክብደት የማህበረሰቡን የመልካምነት ወይም 24 የአድቬንቲስት ቤት የክፋት ሚዛን ከፍ ወይም ዝቅ እንደሚያደርገው የሚያስተውሉ በጣም ጥቂቶች ናቸው።8Messages to Young People, p. 461.AHAmh 23.5

    የጋብቻ ውሳኔ ሲደረግ የተጋቢዎችንና የሚወለዱ ልጆቻቸውን አካላዊ፣ አዕምሮአዊና መንፈሳዊ ደህንነት በሚጠብቅ መልኩ መሆን አለበት። ይህም ወላጆችና ልጆች መሰሎቻቸውን ለመባረክና ፈጣሪያቸውንም ለማክበር የሚያስችላቸው ይሆናል።9Ministry of Healing, pp. 357, 358.AHAmh 24.1

    ወደ ፊት ሚስት ልትሆን የምትችል ሴት ሊኖሩአት የሚገቡ ባህርያት፦ አንድ ወጣት ከጎኑ የምትቆመውን ሲመርጥ የድርሻዋን የሕይወት ሸክም ለመሸከም በልኩ የተሠራች፤ ተጽዕኖዋም የሚያስከብረውና የሚያነጥረው በፍቅርዋም የምታስደስተው መሆን አለባት።AHAmh 24.2

    “አስተዋይ ሴት ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠች ናት።’’ ‘‘የባልዋ ልብ ይታመንባታል….ዕድሜዋን ሙሉ መልካም ታደርግለታለች ክፉም አይደለም።’’ ‘‘አፍዋን በጥበብ ትከፍታለች ያማረም ትምርት በምላስዋ ነው። የቤትዋንም አካሄድ ትመለከታለች የሃኬትም እንጀራ አትበላም። ልጆችዋ ይነሳሉ የተመሰገነችም እንደሆነች ይናገራሉ።’’ ‘‘ባልዋም ያመሰግናታል እንዲህ ብሎ ያመሰግናታል። ብዙ ሴቶች መልካም ያደረጉ አሉ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ’’ እንዲህ ዓይነት ሚስት ያገኘ “በረከት አገኘ ከእግዚአብሔር ዘንድም ፀጋ ይቀበላል።’’ 10Id., p. 359.AHAmh 24.3

    ሊጠኑ ከሚገባቸው ነገሮች መካከል:- የምታገባት ሴት ለቤትህ ደስታን የምታመጣ ትሆናለች? የምጣኔ ሀብት አስተዳደር አዋቂ ናት ወይስ ስታገባት የራስዋን ገቢ መጨረስ ብቻ ሳይሆን የአንተንም ጭምር ከንቱ የሆነ የእዩኝ እዩኝ ምኞትዋን ለማርካት ትጠቀምበታለች? በዚህ ረገድ ያሉት መርሆዎችዋ ትክክል ናቸው? ልደገፍበት የምችለው አሁን ምን ነገር አላት? በጋብቻ ሐሳብና በፍቅር የነሆለለ የወንድ አዕምሮ እነዚህን ጥያቄዎች ምንም መዘዝ እንደሌላቸው አድርጎ ቸል እንደሚላቸው አውቃለሁ። እነዚህ ነገሮች ግን በአንክሮ ሊታሰብባቸው ይገባል፤ ለወደፊት ሕይወትህ ጠቀሜታ አላቸውና!….AHAmh 24.4

    ሚስት ስትመርጥ ጠባይዋን አጥና። ታጋሽና ትጉህ የምትሆን ናት? ወይስ እናትና አባትህ የሚደገፉበት ጠንካራ ልጅ በሚያስፈልጋቸው ሰዓት እንክብካቤዋን ታቆምባቸዋለች? የራስዋን ደስታ ለማመቻቸትና እቅዷን ለማሳካት ስትል ባልዋን ከህብረተሰቡ በማግለል እናት አባቱን አስትታ ወላጆቹ አፍቃሪ ምራት በማግኘት ፈንታ ወንድ ልጃቸውን ያጣሉ?11Letter 23, 1886.AHAmh 24.5

    ወደ ፊት ባል ሊሆን የሚችል ወንድ ሊኖሩት የሚገቡ ባህርያት፦ አንዲት ሴት እራስዋን ለትዳር ከመስጠትዋ በፊት ዕጣ ፈንታዋን የምታቆራኘው ሰው ዋጋ ያለው መሆኑን መመርመርና ማወቅ አለባት። ከዚህ በፊት ያለው ታሪኩ ምን ይመስላል? ሕይወቱ ንጹህ ነው? የሚገልጽላት ፍቅር የከበረና የላቀ ባህርይ ያለው ነው ወይስ እንዲያው ስሜታዊ ፍላጎት ያለው ነው? ባህርይው ደስታ ሊሰጣት የሚችል ተፈጥሮ አለው? በፍቅሩ እውነተኛ ሠላምና ደስታ ታገኛለች? የራስ ማንነትዋን - ከሌሎች የምትለይበት እርስዋነትዋን- እንድትጠብቅ ይፈቅድላታል ወይስ አመለካከትዋንና ንቃተ-ህሊናዋን በባልዋ ቁጥጥር ሥር ማስረከብ ይኖርባታል?ሰውነትና ሕይወት ሐሳብና ዓላማ ንጹህና ቅዱስ ሆነው ይጠበቃሉ? እነዚህ ጥያቄዎች ወደ ጋብቻ ግንኙነት ለምትገባ ሴት እጅግ ብዙ ጠቀሜታ አላቸው።12Testimonies for the Church, Vol. 5, p. 362.AHAmh 24.6

    ከወደፊቱ ስቃይና እሮሮ ለማምለጥ የምትሻ፤ ትዳርዋ በሠላምና በደስታ የተሞላ እንዲሆን የምትፈልግ ሴት ለፍቅር ከመረታትዋ በፊት እንዲህ ብላ ትጠይቅ:- አፍቃሪዬ እናት አለው? የባህርይዋ ማህተም ምን ይመስላል? ለእናቱ ላለበት ኃላፊነት እውቅና ይሰጣል? ፈቃድዋን የሚያከብር ለደስታዋ ግድ የሚለው ነው? ለእናቱ ክብር የማይሰጥ ከሆነ አክብሮትና ፍቅር ደግነትና ትኩረት ለሚስቱ ማሳየት ይችላል? የአዲስ ሙሽርነታችን ስሜት ሲያልቅ አሁንም ያፈቅረኛል? ስሳሳት ይታገሰኛል? ወይስ ነቃፊ፣ ጨቋኝና አምባ-ገነን ይሆንብኛል? እውነተኛ ፍቅር ብዙ ጥፋቶችን አይከታተልም - ፍቅር እነዚህን አያስተውላቸውም።13Fundamentals of Christian Education, p. 105.AHAmh 25.1

    ንጹህ የወንድ ባህርይን ብቻ ተቀበይ፦ አንዲት ወጣት ሴት እንደ ትዳር አጋር አድርጋ የምትቀበለው ሰው ንጹህና የወንድ ባህርይ ያለው ጠባይ የያዘ፣ ትጉህ፣ ህልም ያለው፣ ታማኝ፣ እግዚአብሔርን የሚወድና የሚፈራ ዓይነቱን ብቻ ይሁን።14Ministry of Healing, p. 359. AHAmh 25.2

    አክብሮት ከጎደለው ከእርሱ ራቁ። ስንፍናን ከሚወድ አምልጡ፤ በተቀደሱ ነገሮች ላይ ከሚያፌዝ ተጠበቁ፤ የብልግና ንግግር ከሚናገር ጓደኝነት ወይም አንድ ብርጭቆ ብቻ አስካሪ መጠጥ እንኳ ከሚጠጣ ሽሹ፤ ለእግዚአብሔር ያለበትን ኃላፊነት ለማያውቅ ወንድ የጋብቻ ጥያቄ ጆሮአችሁን አትስጡ። በጣም ደስ ከሚያሰኛችሁ ጓደኝነት፣ ሆኖም እግዚአብሔርን ከማይፈራና ከማይወድ፣ ስለ እውነተኛ ጽድቅና ቅድስና መርሆዎች ምንም ከማያውቅ ወዳጅነት መላቀቅ ትችሉ ዘንድ ነፍስን የሚቀድሰው ንጹህ እውነት ብርታት ይሆናችኋል። የጓደኞቻችንን ጉድለቶች ሁልጊዜ ልንታገስ እንችላለን፤ ሴሰኝነትንና የዝሙት-ባህርይን መሸከም ግን ፈጽሞ አይሆንልንም።15Letter 51, 1894.AHAmh 25.3

    ጥፋት መሥራት ከማረም ይቀልላል፦ ብዙ ጊዜ በችኮላና በራስወዳድነት የታቀዱ ጋብቻዎች መልካም ውጤት አይኖራቸውም፤ በአሰቃቂ ውድቀት የሚደመደሙ ናቸው። ሁለቱም እራሳቸውን ተታልለው ያገኙታል፤ በስሜት ያደረጉትን ነገር ሊለውጡት ቢችሉ በወደዱ ነበር። በዚህ ዙሪያ ጥፋት ከተሠራ በኋላ ጥፋቱን ለማስተካከል ከሚደከመው ድካም ጋር ሲነጻጸር ጥፋት መሥራት ቀላል (በጣም ቀላል) ነው - ጥፋት ከእርማት ይቀልላል።16 Letter 23, 1886.AHAmh 25.4

    ጥበብ የጎደለውን እጮኝነት ማቋረጥ ይመረጣል፦ ልታገቡት ያሰባችሁት ሰው ባህርይው በትክክል ሳይገባችሁ ቀለበት አስራችሁ ከሆነ እጮኝነታችሁን እንደ ግዴታ ቆጥራችሁ የጋብቻ ቃል-ኪዳን በመፈፀም ሊያፈቅራችሁና ሊያከብራችሁ ከማይችል ሰው ጋር ለመቆራኘት እንዳታስቡ ተጠንቀቁ። እንደ ሁኔታው ወደሚባል እጮኝነት እንዳትገቡ ተጠበቁ፤ ብዙዎች እንደሚያደርጉት ከጋብቻ በኋላ ከመለያየት እጮኝነቱን ማፍረስ በጣም፣ እጅግ በጣም ይሻላል።17Fundamentals of Christian Education, p. 105.AHAmh 25.5

    እንዲህ ልትሉ ትችላላችሁ፡- “ቃል ገብቻለሁ አሁን ታዲያ እንዴት ቃሌን ልጠፍ?’’ የእኔ መልስ፡- ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጻረር ቃል ገብታችሁ ከሆነ በምንም ዓይነት ሳትዘገዩ አፍርሱት። በትህትና በእግዚአብሔር ፊት ቀርባችሁ እንዲህ በችኮላ ቃላችሁን እንድትሰጡ አድርጎ ያነሆለላችሁን ነገር ተናዘዙ። እንደዚህ አይነቱን ቃልኪዳን ከምትጠብቁና በኋላ ፈጣሪያችሁን ከምታሳዝኑ አሁን በፈሪሐ-እግዚአብሔር ብታፈርሱት እጅግ የተሻለ ነው።18Testimonies for the Church, Vol. 5, p. 365.AHAmh 26.1

    ወደ ጋብቻ ህብረት የሚመራው እያንዳንዱ እርምጃ በመጠን መሆንን፣ ግልጽነትን፣ ልባዊነትን እንዲሁም ቅንነት የተሞላበት እግዚአብሔርን የማስደሰትና የማክበር ዓላማ ያነገበ መሆን አለበት። ጋብቻ በዚህ ዓለምና በሚመጣው ዓለም ሕይወታችን ተጽዕኖ የሚያሳድር ነው። እውነተኛ ክርስቲያን እግዚአብሔር የማያጸድቀውን እቅድ አይነድፍም።19Ministry of Healing, p. 359.AHAmh 26.2